Thursday, January 9, 2014

ሰማያዊ ፓርቲ ሀሳቡን በኢሳት ላይ ለመግለጽ የማንንም ይሁንታ እንደማይጠይቅ አስታወቀ

http://ethsat.com/amharic
ታህሳስ ፴ (ሰላሳ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ፓርቲው ” የምንናገርበትን የመገናኛ ብዙሃን ማንም እንዲመርጥልን ወይም እንዲወስንልን አንፈቅድም” በሚል ርእስ ባወጣው የአቋም መግለጫ፣ ” ሰማያዊ ፓርቲ መልዕክቱን የሚያስተላልፍበትን መገናኛ ብዙሃን ማንም አካል እንዲመርጥለት ወይም እንዲወስንለት የማይፈልግ መሆኑን ግልፅ ” አድርጓል።
“በሕገ መንግስቱ የተረጋገጠውን ማንም ሰው በመረጠው መንገድ ሃሳቡን የማስተላለፍ መብቱን በመጠቀም በኢሳትም ሆነ እድሉን ካገኘ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን አቋሙንና እምነቱን ማስተላለፍ የሚቀጥል መሆኑን ማረጋገጥ ይወዳል” በማለት ፓርቲው በኢሳት ላይ ቀርቦ አቋሙን ከመግለጽ እንደማይገታ ግልጽ አድርጓል።
ሰማያዊ ፓርቲ ታህሳስ 25 ቀን 2006 ዓም በኢቲቪ የተላላፈውን ዶክመንታሪ ፊልም “የእብሪት መልዕክት” ያዘለና እና “ከተራ ርካሽ ፕሮፓጋንዳነት የማያልፍ የሕግና የዲሞክራሲያዊ መብት ገደብን ካለማወቅ የሚመነጭ አስተሳሰብ ነው” ሲል አጣጥሎታል።
“የብሔራዊ ደህንነት መረጃ እና የፀረ ሽብር ግብረ ኃይል  በተደጋጋሚ ጊዜ በሽብር ወንጀል ጠርጥሬአቸዋለሁ የሚላቸውን ሁሉ በመክሰስ ወደ እስር ቤት እንዲወርዱ እያደረገ ጉዳያቸው የፍርድ ቤት ውሳኔ ሳያገኝ እንደፈለገ በሚቆጣጠረው ወይም በሚያዘው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ሬዲዮ ድርጅት አማካኝነት የፈለገውን ዓይነት ፍረጃና ሥም ማጥፋት ሲያካሒድባቸው” መቆየቱን ያስታወሰው ሰማያዊ ፓርቲ፣ ይህ ራሱን ከሕግ በላይ የሰቀለ አካል ያለምንም ገደብ ከሚሰራቸው ተግባራት እንዲታቀብ በሕግ የሚያስቆመው በመጥፋቱ እስካሁን የፈፀማቸውን የማንአለብኝነት ተግባራት እንደጥፋት ሳይሆን እንደ መልካም ሥራ ቆጥሯቸው በተመሳሳይ የሥም ማጥፋትና የፍረጃ ተግባሩ እንዲገፋበት አድርጎታል” ብሎአል።
“ኢሳት” የተባለ የመገናኛ ብዙሃን በኢትዮጵያ መንግስት በሽብርተኝነት ከተፈረጀ ድርጅት የገንዘብ ድጋፍ እንደተደረገለትና በሰላማዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱ ድርጅቶች በተለይም ሰማያዊ ፓርቲ በዚህ የመገናኛ ብዙሃን እንዳይጠቀም የማስጠንቀቂያ ዛቻ ተላልፎለታል” ሲል ያስታወሰው ሰማያዊ ፓርቲ፣  ይህ አስፈራሪ አካል ራሱን ሕግ አውጭና ሕግ ተርጓሚ በማድረግ የዚህች ሐገር ዜጎች ሃሳባቸውን የሚገልጹበትንና የማይገልጹበትን የመገናኛ ብዙሃን እየወሰነላቸውና እየመረጠላቸው ይገኛል፣ ብሎአል ።
የገዥው ቡድን ሰዎች ሀሳብን በሃሳብ ማሸነፍ እንደማይችሉ ስለሚያውቁት የቀራቸው አማራጭ ዲሞክራሲያዊ ኃይሎች ሃሳባቸውን የሚያሰራጩባቸውን መንገዶች መዝጋት ብቻ መሆኑን ፓርቲያችን ይገነዘባል ያለው ሰማያዊ ፓርቲ፣  ማንም አካል በሕግም ሆነ በሞራል ተጠያቂ የሚሆነው የሚያስተላልፈው መልዕክት ይዘት የሌሎችን ዲሞክራሲያዊና ሞራላዊ መብት የሚጋፋ መሆን አለመሆኑ እንጂ ገዥው ቡድን በጠላው ወይም በወደደው የመገናኛ ብዙሃን መልዕክቱን ማስተላለፉ አይደለም” ሲል አቋሙን ግልጽ አድርጓል፡፡ መልዕክትን የገዥው ቡድን ሰዎች በጠሉት የመገናኛ ብዙሃን ማስተላለፍ በራሱ ወንጀለኛ ወይም ሽብርተኛ ለማድረግ የሚያበቃ ምንም ዓይነት የሕግ መሰረት እንደሌለውም ገልጿል፡፡
ፓርቲው በመጨረሻም ” ሰማያዊ ፓርቲ መልዕክቱን የሚያስተላልፍበትን መገናኛ ብዙሃን ማንም አካል እንዲመርጥለት ወይም በዚሁ አጋጣሚም የፓርቲያችንን መልካም ስም በሃሰት ለማጉደፍ የተሰነዘሩ ቃላትን በቀላሉ የማንመለከታቸው መሆኑን ሕግ ባለበት ሐገር ራስን ከሕግ በላይ በማስቀመጥ ማንንም አካል መፈረጅና ስም ማጉደፍ በሕግ የሚያስጠይቅ መሆኑን የዘጋቢ ፊልሙ ባለቤቶች እንዲያውቁትና ወደፊትም ተመሳሳይ ድርጊት ከመፈፀም እንዲቆጠቡ እናሳስባለን፡፡” ብሎአል።
በአገር ውስጥ የሚንቀሳቀሱት ሰማያዊ ፓርቲ እና አንድነት ፓርቲ በኢሳት ላይ ቀርበው አቋማቸውን እንዳይገልጹ መንግስት ሰሞኑን ምክር አዘል ማስጠንቀቂያና ማስፈራሪያ በኢቲቪ አማካኝነት መስጠቱ ይታወሳል።
ከመጪው ምርጫ ጋር ተያይዞ ኢሳት ገዢውን ፓርቲ ጨምሮ በአገር ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች ፕሮግራሞቻቸውንና መልእክቶቻቸውን በነጻ እና ያለገደብ የሚያስተላልፉበትን አሰራር በመቀየስ ላይ ነው።

Wednesday, January 8, 2014

አንድነት – አቶ አለማየሁ ለሴቦ፣ የአንድነት ፓርቲ አባል በሲዳማ ታሰሩ





https://www.andinet.org

አቶ አለማየሁ ለፌቦ የተባሉ የአንድነት ፓርቲ አባል፣ ከፓርቲው ጠቅላላ ጉባኤ ማግስት ወደ ክልሉ ሲመለሱ እንደተያዙ ለማወቅ ተችሏል። ፖሊሶቹ እንደ ክስ ያቀረቡት ነገር፣ «የፓርቲውን ሰነድ በወረቀትና በኮምፒዩተርህ ውስጥ ተገኝቷል» የሚል እንደሆነ ለማወቅ ችለናል፡፡ አቶ አለማየሁ በምርጫ ቦርድ ተመዝግበው፣ ህጋዊ በሆነ ፓርቲ መሳተፉቸውና ስብሰባ ላይ መገኘታቸው ምን ዓይነት ወንጀል እንደሆነ ለማጣራት ወደ ሌንሳቦ ወረዳ ወርቃ ከተማ ብንደውልም አስተያየት የሚሰጠንን አላገኘንም፡፡
እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ ህገ-መንግስት ማንም ሰው በየትኛው ህጋ ድርጅት ውስጥ መሳተፍና መጀራጀት እንደሚችል፣ የሀሳብ ነፃነት እንዳለው፣ ያንንም ማንፀባረቅ እንደሚችል ተደንግጓል፡፡ እየሆነ ያለውና በአቶ አለማየሁን ለእስር ያበቃው ግን እጅግ ከዚህ ጋር የሚጋጭ ነው፡፡ አቶ አለማየሁ በአሁኑ ሰዓት በዕስር ላይ የሚገኙ ሲሆን ተጨማሪ መረጃ እየተከታተልን እናቀርብሎታለን፡

አንድነት ፓርቲ ለሚዲያዎች ሃሳብን መግለጽ አሸባሪነት አይደለም አለ

ታህሳስ ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ ባወጣው መግለጫ ሰሞኑን ኢቲቪ ባዘጋጀው ዶክመንተሪ ላይ “መቀመጫውን በውጭ በማድረግ የተለያዩ ዜናዎችንና ፕሮግራሞችን በማሰራጨት የሚታወቀውን ኢሳት(ESAT) ሬዲዮ እና ቴሌቪዥን ጣቢያ ላይ ፓርቲያችን ለአባላቱ እና ለደጋፊዎቹ መልዕክት ማስተላለፉን እንዲሁም እንደፓርቲ ለማንኛውም ሚዲያ የፓርቲያችንን ሰላማዊ እንቅስቃሴ በተመለከተ ስንጠየቅ የመመለስ መብታችንን በሚጋፋ መልኩ የፓርቲያችንን አቋም አዛብቶ ለማቅረብ ሞክሯል” ብሎአል፡፡
“ኢህአዴግ በሚጠላቸው እና በሚያጥላላቸው ሚዲያዎች ሃሳብን መግለፅ በየትኛውም መመዘኛ አሸባሪነት ሊሆን አይችልም” ያለው አንድነት፣  የኢህአዴግ መንግስት ሲያስነጥሰው ከሚያለቅሱለት የፕሮፓጋንዳው ፍጆታዎች ከሆኑት ሚዲያዎች ውጪ የኔ ያልሆኑ የሌላ ናቸው ብሎ የሚያምን በመሆኑም ፍረጃው ህጋዊ አግባብነትም ሆነ መረጃ የሌለው ባዶ ፍረጃ ” ነው በማለት የመንግስትን ማስጠንቀቂያ አጣጥሎታል።
“ኢህአዴግን  የህዝብን ጥያቄ በዶክመንተሪ ጋጋታ መመለስ እንደማይቻል” ልናስታውሰው ብንሞክርም፣  አሁንም በዶክመንተሪ ፊልሞች ስም ከማጥፋት፣ ከመፈረጅና ከማስፈራራት መላቀቅ አልቻለም፡፡ ” ሲል ፓርቲው አክሎ ገልጿል።
አንደነት በመጨረሻም ” ህገ መንግስታዊ መሰረት የሌለው ቢሆንም እንኳ ቢያንስ ራሳቸው ላወጡት ህግ ታምነው ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በማቅረብ ሳያስወስኑ አንድን የሚዲያ ተቋም ያውም ለአንድ አላማ የተቋቋመ የፀረ-ሽብር ግብረሃይል ‹‹የአሸባሪ ድርጅት ልሳን ነው›› ወይም ‹‹አሸባሪ ነው›› በማለት ሲፈርጅ ስናይ አሁንም የሀገራችን ፖለቲካ ፓርቲና መንግስት የተደበላለቁበት፣ አንድ ድርጅት እንደፈለገው የሚፈርጅበት ስርዓት እንዳለ የሚጠቁም ነው” ብሎአል፡፡

People think Ayalew resigned due to reasons related to Border issue, Gov’t study finds

ESAT News
January 7, 2014
A new study conducted by the Public Opinion Information Section of the Government Communication Affairs Office has found that the resignation of Ayalew Gobeze, the ex-president of the Amhara Regional State, is a strategy by the government to better carry out the border demarcation between Tigray and Amhara regions.  Ayalew Gobeze resigned from his post last month and was succeeded by his Deputy Degu Andargachew in what the government called a ‘power succession’.
According to the information collected Degu Andargachew is not well received by the populace. Many believe that he is only there to execute the plans and demands of the Tigrean People’s Liberation Front (TPLF).
Similarly, Ahmed Abetew, former Deputy Administrator and currently Ethiopia’s Trade Minister, and Alemnew Mekonen, Head of the Amhara National Democratic Movement (ANDM) Secretariat are both labelled as loyal to the TPLF. Insiders told ESAT that the two officials have been discovered possessing two Eurotracker vehicles; they have not been removed from their positions due to their loyalty to the TPLF.
During a cabinet evaluation, the two officials had said that the two vehicles were given to them by Chinese Companies in consideration of their ‘leadership qualities’. According to the Office there was no opinion given ‘benignly’. The opinions will presented to the Government’s Information Section and the Cabinet will discuss on it.

Monday, January 6, 2014

የቴዲ አፍሮ ኮካኮላ ውል እንዲሰረዝ ዘመቻ ተጀመረ

 http://ecadforum.com/Amharic/archives/10659/
January 6, 2014

ኢትዮጵያውያን ዝምታውን በመስበር የሶሻል ሚድያ ዘመቻ መክፈት ይገባቸዋል

በ2014 ብራዚል ለሚካሄደው የአለም ዋንጫ ላይ ቴዲ አፍሮ የክብር እንግዳ እንዳይሆን አዲስ ዘመቻ በእነ ጃዋር መሃመድ መጀመሩ ተሰማ።Coca-cola a global leader in the beverage industry
በዓለም ዙርያ ያሉ ኢትዮጵያውያን በሳውዲ ለተፈናቀሉ ወገኖች እየተረባረቡ ባሉበት በዚህ ፈታኝ ወቅት፤ ጃዋር እና ሜንጫዎቹ ጸረ-ኢትዮጵያዊነት ዘመቻቸውን በስፋት ተያይዘውታል። በዛሬው እለት ከአዲስ አበባ በደረሰን ዜና መሰረት ኮካኮላ የቴዲ አፍሮን የአለም ስፖርት ፌዴሬሽን (ፊፋ) ስፖንሰርነት እንዲያነሳ ጠይቀዋል። አዲስ አድማ ለመጀመርም ዝግጅታቸውን አጠናቀዋል።
በ2014 ብራዚል ለሚካሄደው የአለም እግር ኳስ ዋንጫ አፍሪካን ወክሎ እንዲገኝ ኮካኮላ ቴዲን የመረጠው መሆኑ ይታወሳል። የአለም ስፖርት ፌዴሬሽን (ፊፋ) ወጣቱ ቴዲ አፍሮ አፍሪካን እንዲወክል መምረጡ ዘረኞቹን አስቆጥቶ እንደነበር የሚታወስ ነው።
ቴዲ አፍሮ በአለም መድረክ ላይ የሚያቀርበው ኢትዮጵያዊ የሙዚቃ ቃና ሀገራችንን እና መላው አፍሪካን የሚያስጠራ ነው።
የሄነከኑ አድማ በኦህዴድ ብርቱ ጥረት የተሳካላቸው እነኚህ ባለ አድማዎች፣ ሰሞኑን የደስታ መግለጫቸውን በየድረ-ገጾቻቸው ላይ እየተለዋወጡ እንደሆነ ተገልጿል። ሄኒከን ኮንሰርቱን የሰረዘው ከኦህዴድ በተላለፈ ቀጭን ትእዛዝ ስለመሆኑ ማስረጃው አሉ።
እነ ጃዋር በዚህ አላበቁም። በዲሴምበር 8፤ 2013 በተላለፈ የአቶ ቡልቻ ደመቅሳ እና ሌሎች ምሁራን ቃለ-ምልልስ ምክንያት የጀርመኑ (ዶቸ ቨለ) የአማርኛ ድምጽ ሬዲዮ ጋዜጠኛ ከስራ እንዲነሳም ከአቤቱታ ጋር ቀጭን ትእዛዝ ለቦርዱ አስተላልፎ ነበር። የዶቸ ቨለ ቦርድ ላይ ኦህዴድ ተጽእኖ ስለሌለው ይህ ዘማቻ ሊሳካ አልቻለም።
የኮካኮላው ዘመቻ የተነጣጠረው በቴዲ አፍሮ ላይ ሳይሆን በአኢትዮጵያዊነት ላይ ስለሆነ በአለም ዙርያ ያሉ ኢትዮጵያውያን ዝምታውን በመስበር በነዚህ ሰዎች ላይ የሶሻል ሚድያ ዘመቻ መክፈት ይገባቸዋል።

በምነው ሸዋ ኢንቴርቴንመንት አማካኝነት ወደ አሜሪካ የመጣው ሀንቻሱ ሁንዴሳ የተባለው ዘፋኝ በሚካሄዱት ኮንሰርቶች ላይ ከፍተኛ ጸረ ኢትዮጵያ ዘመቻ ከፍትዋል

 http://www.boletoday.com/shewa/
በምነው ሸዋ ኢንቴርቴንመንት አማካኝነት ወደ አሜሪካ የመጣው ሀንቻሱ ከፍተኛ የኢትዮጵያ ጥላቻ ያላቸው ያለው ግለሰብ ከመሆኑም በላይ አማርኛን ማውራት የማይወድና ሌሎችን ኢትዮጵያውያን በተለይም አማራውን በከፍተኛ ጥላቻ የሚያይ ነው ::በቅርቡ በየስቴቱ በተካሄደው ኮንሰርት ላይ ይህንን ጥላቻ የሚያሳዩ ጥላቻን ሚዘሩና እልቂትን ሚጋብዙ ዘፈኖችን ሲጫውት  በተደጋጋሚ ታይትዋል:: የምነው ሸዋ ባለቤት ዝምታን የመረጠው ኦሮሞ ስለሆነ ወይስ ጉዳዩን ስላላወቀ እንደሆነ ለማወቅ አልተቻለም::

hqdefault-1

mqdefault

Sunday, January 5, 2014

የማይመስል ነገር ለሚስትህ አትንገር! ኢቲቪ ስለ ኢሳት


http://ecadforum.com/Amharic/archives/10645/
January 4, 2014
ቢታኒያ አለማየሁ፣ አዲስ አበባ

ዶክመንታሪ ብሎ ዝም! አስቡት እስኪ ኢህአዴግን በሚያክል አፋኝ መንግስት በኢቲቪ ኢሳት ሲብጠለጠል፣’ኢሳት ማለት የኢትዮጵያ ህይዝብ እውነተኛ የመረጃ ወፍጮ ነው!’Ethiopian Satellite Television (ESAT)

ለምን ግን በዚህ ሰአት ስለ ኢሳት ዶክመንታሪ መስራት አስፈለገ?
-ኢሳት ከተመሰረተ አንስቶ እስካሁን ድረስ በእውነተኛ መረጃ ምንጭነት በመላው የኢትዮጵያ አንጀት ውስጥ ተደላድሎ መቀመጡን ስልሚያውቁ!
-ይከስማል ይጠፋል አቅሙ ይዳከማል ሲሉት እንደ ወይን ጠጅ ከለት እለት እየበሰለና እየጎመራ መምጣቱን ስላዩ!
-በመላው ኢትዮጵያ የሚገኙ ተምልካቾች ለኢሳት በመደወል በሚሰጡት አስተያየት ህዝቡ በሚገባ እየተከታተለው መሆኑን ስላረጋገጡ!
-ከዚህ ቀደም ከሰባት ጊዜ በላይ ጃም በማደርግ እና በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ኢሳት ወደ ኢትዮጵያ የሚያደርገውን ስርጭት ቢያቛርጡም ኢሳት ግን የተለያዩ የሳተላይት አማራጮችን በመጠቀም ከአንድ አመት በላይ(እስካሁን) ያለ ምንም ችግር ወደ ኢትዮጵያ ማሰራጨ ስለቻለና አሁን ካለው የኢኮኖሚ ሁኔታ አንጻር ጃም ማድረግ ከፍተኛ ወጪ ስለሚጠይቅ!
-ህዝብን አደንቁሮ በኢቲቪ ፕሮፓጋንዳ ብቻ የህዝብን አምሮ ለማደደብ በሚደርገው ጥረት ኢሳት ነጻ ሃሳብ በማነሸራሸር እንቅፋት ስለሆነ!
ባጠቃላይ ኢሳት ለህዝብ እውነትን በመግለጽ ለስረአቱ የእግር እሳት መሆኑ ስለታመነበት:- የኢሳትን ይዘት ተንትኖ እና እውነቱ ይህ ሆኖ ሳለ ኢሳት ግን እንዲህ ይላል በሚል አመክኖዋዊ አስተሳሰብ ከመሞገት ይልቅ፣ ግንቦት ሰባት አሸባሪነው ኢሳት ደግሞ የግንቦት ሰባት ነው ስለዚህ ኢሳት አሸባሪ ነው ብለው ከደመደሙ በኋላ ህዝቡ አሳትን መከታተል እንደ ሽብርትኛነት አድርጎ ቆጥሮት መከታተሉን እንዲያቆም ለማግባባት ቀጥሎም ለማስገደድ ያመች ዘንድ የተሰራ ድራማ ነው! የዘፈን ዳር ዳሩ እስክሳ ነው ትል ነበር አያቴ! የሚገርመው ግን አቶ ሃይለማሪያም እንዳሉት “ግንቦት ሰባት በቅዠትላይ የተመሰረተ ድርጅት” ከሆነ ይህን ያክል ተከታታይ ድራማዎች በመስራት ምን አደከማቸው? በራሱ ጊዜ ከእንቅሉ ይባንንላቸው የለም እንዴ?
እናንት አሸባሪ ኢሳቶች ሆይ ህዝብን እልል እያስባላችሁ አንባገነኖችን እያሸበራችሁ ነውና በርቱ! በርቱ! በርቱ!
ቢታኒያ አለማየሁ


Wednesday, January 1, 2014

ኣወይ ጉዴ ወይ መላ ጉዴ (ሄኖክ የሺጥላ)

  http://ecadforum.com/Amharic/archives/10605/

January 1, 2014
ሄኖክ የሺጥላ
ኣወይ ጉዴ ወይ መላ ጉዴ
ብቸኛው ልቤ ሰው  በመውደዴ
ነው  ያለው ኣረጋሃኝ ወራሽ ኣሁን እንደሱ ልፋትና ጥረት ቢሆን ኖሮ የኢትዮጵያ ሙዚቃ የት በደረሰ። ለነገሩ ይሄ ትውልድ የተሰራውን ሁሉ በመናድ : የተጣፈውን ሁሉ በመካድ ነው የሚታወቀው። እኔ እንኳ በዘመኔ ስንት ኣየሁ። ኣሁን ማን ይሙት ኣደይ ትርሃስ በፍራሽ መዋጥ ለሁለት ዕየከፈሉ ያጸኑት ሹሩባ የሚረሳ ሆኖ ነው “ቢዮንሴ ሄር ስታይለር ምናምን ምንምን በሚል ሰጋቱራ ሃገሩን ያጥለቀለቅነው።” እስኪ ኣሁን ምን ትውልድ ኣለ። ድሮ ቡና እንኩዋ እስከ ሶስተኛ ነበር የሚጠጣው፤ ኣሁን ግን ኢኮኖሚው በ ፲፩ ፐርሰንት ኣድጎ ቡና እንኩዋ የሚያቆመው ሰባተኛ ምናምን ላይ ነው። በውነት ፕሮፌሰር ኣልማርያም እንደሚሉት ይሄ ትውልድ ኣቦ ሸማኔ ሳይሆን ኣቦል ሸማኔ ነው። ኣያቶቻችን ለኣድዋ ጦርነት ምታ ነጋሪት ክተት ሰራዊት ሲሉ፤ መለከት: ጥሩንባ ሲነፉ  ነው ታሪክ የሚነግረን። ዛሬ ግን የመለከት እና የእንቢልታ ሪሚክስ  በየ ስርጣ ስርጡ ሺሻ መንፋት ሆኖዋል ግብራችን። የሰሞኑ መፈክር ኪንግ ኣብደላ ሼም ኦን ዩ፤ ሼም ሼም ሼም፤ ነበር ኣይደል፤ ምነው ሺሻው ተረሳ ታዲያ፤  ኣጎቶቻችን  ባርነትና ውርደት ብቻ ሳይሆን ሱሰኝነቱንም ኣወረሱን።Ethiopian poet Henok Yeshitla
እንግሊዚኣዊው  ጋዜጠኛና ጠሃፊ Grham Hancook The sign and the Seal (The Quest for The Lost Arc of the Covenant)  በሚለው መጥሃፉ ላይ The Ethiopian slept a thousand years forgetting the world by whom they were forgotten by  ይላል :: በነገራችን ላይ የላይኛውን የኣነባበብ ዘዬ (style ) ኣንድ ነገርን ኣስታወሰኝ :: ባንድ ወቅት በስድስት ኪሎ (university ) ያስተምሩ የነበሩ መምህር  ስለ ጆነፍ ኬንዲ ሞት ለተማሪዎቻቸው ሲያስተምሩ (During the time and death of Jonneif Kennedy everybody was shocken) ኣሉ በዚህን ጊዜ ኣንድ የቅዱስ ዮሴፍ ተማሪ ሳቁን ለሞአቆጣጠር ሲታገል  ያስተዋሉ እኝሁ መምህር በነገሩ በስጨት ይሉና “ምን ያስቅሃል ሾካካ!!!” ኣሉ ኣሉ። እንግዲህ ያዙልኝ ሾክን ሾካካ ከሚለው ነው የመጣው ማለት ነው። እሺ ይሁን  ሾክንስ ከሾካካ ነው እንበል፤ ኣድርባይነት፤ ባንዳነት፤ ሆዳምነት፤ ታሪክ ሸቃይነት፤ እነዚህስ?  ኣንድ ወዳጄን በጣም በስጨት ብዬ ኣረ ባክህ እኔ ኣልገባኝም ይሄ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን መናቅ ከየት የመጣ ባህል ነው ስለው፤ ፈገግ ብሎ በርግጠኝነት ከቻይና ኣይደለም፤ ከቻይና ቢሆን ይህን ሁሉ ዘመን ኣብሮን ኣይቆይም ነበር፤ ማናልባት ከጣልያን ይሆን እንዴ ኣለኝ። ወይ ኢትዮጵይ፤ ልጆችሽ ተከብረሽ የኖርሽው ባባቶቻችን ደም የሚለውን ዘፈን  በየስብሰባው እና ሰላማዊ ሰልፉ ላይ ደጋግመው በማቀንቀናቸው ዘፈኑ ራሱ ሰልችቶት ልጆቼ ሃያ ሶስት ኣመት ደከመኝ ሰለቸኝ ሳልል ተዘፈንኩላችሁ በሉ ኣሁን ሌላ ዘፈን ፈልጉ፤ እናንተን እንዳየሁዋችሁ ከሆነ ፤ እኔን እንደ ልደት ዘፈን በሻማ ከባችሁ ከማልቀስ ውጪ  ምንም የምታመጡ ኣይመስለኝም፤ እና ጡረታዬን ጠብቁልኝና እስኪ ደሞ ይቺ የቀረችው ጊዜዬን እፎይ ብዬ ልኑር ኣለ ኣሉታዲያ ምን ይዋጠን፤ ኣንቺም ዜሮ ዜሮ እንዳንል ዘፋኙ እንጀራው ላይ የቅንድብ ጠጉር ተገኝቶበት ገበያውን ገደለው፤ ምን ይበጀን፤ ምን ይሻለን።  ከማቀንቀን ውጪ ሌላ ነገር ለማድረግ ዛሬም በቅጡ የተዘጋጁ ኣይመስልም፤ በየ ዝግጅቱ ላይ ኣበው ኣባቶቻችንን በ ፩ ደቂቃ የህሊና ጸሎት ከማሰብ ውጪ ሰምሮላቸው የተሻለ ነገር ሲያደርጉ ዛሬም ኣናይም።
ወደ ግራሃም ሃንኩክ ልመለስ…ኣዎ “The Ethiopian Slept…. A 1000 years forgetting the world by whom they were forgotten by.”
(ይህንን ፈረንጅኛ በኣማርኛ ብናራምደው ወይም ወደ ኣማርኛ ብንቀዳው) ኢትዮጵያዊያኖች ኣለምን ረስተው ኣለምም እነሱን ረስታ ለሺ ኣመተታት ኣንቀላፉ)ማለት ይሆናል።  ታዲያ የዚህን ሰውዬ ኣባባል የነብይ ግብር ለመስጠት ኢስቲመስል ድረስ ዛሬ ሃገሪቱ ኣልጋ በኣልጋ ሆናላች። ኣዎ ለኢሃዲግ መራዡ (ይቅርታ መራሹ መንግስት ኣልጋ ባልጋ) ከዚህ ካለሁበት ኣማሪካም ይሁን ከኣውሮጳና ከሩቅ ምስራቅ ሃገራት ለሳምንታት ተንፍሰው መምጣት ለሚፈልጉት  ኣቦ ሸማኔዎችም ኣልጋ በኣልጋ። ኣንቺ ሃገር ያለው ዘፋኝ ማን ነበር። ማንስ ቢሆን ምን ዋጋ ኣለው።
ታላቁ የኢሃዲግ መንግስት ከሚከበርበትና ከሚወደስበት የቀለበት መንገድ በተጨማሪ (ግድቢ ኣደይ ሃዳስ (የእማማ  ሃዳስ ግድብ) (ለመሃል ኣገር ሰው ይስማማ ዘንድ የህዳሴውን ግድብ እየተባለ የሚነገረውን  ሳይጨምር…) ከሚታወቅበት ኣንዱ እንቅልፍን ያለ ገደብ መፍቀዱ ነው።  በነገራችን ላይ ያባይ ቦንድ የብዙ ኣባወራዎችን ትዳር በማፍረሱ ያባይ ቦንብ የሚል ስም ሊሰጠው እንደሆነ ጥቃት ያደረሱትም ጥቃት የደረሰባቸውም እየተናገሩ ነው:: የዚህ ያባይ ቦንብ የሽብር ጥቃት ሰለባ የሆኑት ሰዋች እንደሚሉት ከሆነ ኣማሪካ ቢሆን disability  ክሌም ኣርገን እንደ ኣካፋ ዝቆ በሚያነሳ ኣውቶብስ ፈልሰስ እያልን እንኖር ነበር፤  እኛ ግን ከጥቃታችን ሳናገግም፤ ተገድቦ የት ያደርሰናል ያልነው ኣባይ ጉሮሮዋችንን ገድቦ ይስረቀረቃል ብለዋል። ለነገሩ ኣባይ ኣፍ የለውም እንጂ ቢጠይቁት የደደቢት ድርዬዎች ሃንግ ኣረጉኝ ብሎ ለኣውሽና ቦርከና ይናገር ነበር። ምን ያረጋል ታዲያ ኣባይ እንኩዋን ኣፍ ማደሪያ የለውም። ኣባይ በስምሽ ስንት ታሪክ ተሰራ። ትገርሚያለሽ፤ በቃ ግንዱ ኣልበቃ ብሎሽ የዲያስቦራን ዶላር ትጠርጊ ጀመር፤ ለነገሩ ኣንቺ ምን ታረጊ፤ ሆዶ ነው ቁም ነገረኛ ያረገሽ እዚህ ዛሬ ከኛ ጋ ተቃውሞ ማታ ደሞ እትዮጵያ ደውሎ፤ እንዴት ነው ቦንዱ፤ ግድቡ እያለቀ ነው፤ ምን ይጠበቅብኛል ጌቶች የሚለው፤ ይሄ ሁለት ቢላ ህዝብ ኣባይዬ በናትህ በጣና ይሁንብህ፤ ይህንንማ ውስክስክ ላፍልኝ፤ መቅኖ ኣስቀረው፤ ኣላርፍ ያለ ዲያስፖራ ያባይ ቦንድ ይገዛል ኣሉ።
የጎጃም ገበሬ እንኩዋ  ዛሬ ቦንድ ካልገዛህ ኣባይ ኣጠገብ ዋሽንት መንፋት ኣትችልም ሊባል እንደሆነ ሰምቼኣለሁ፤ ዋሽንቱስ ይሁን፤ ቢያንስ ውሃ ሽንት ይፍቀዱላቸው።
በኣባይ ቦንድ መሸወዳቸው የገባቸው ኣንዳንድ ግለሰቦች በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ቀርበው  ሲናገሩ እንደሰማነው ከሆነ “ቦምብን በቦንድ ስም መንግስት ሲያስታጥቀን ዝም ብሎ የተመለከተው ሰማያዊ ፓርቲ ይጠየቅልን ብለዋል።” ጉዳዩን ሲከታተል የነበረው መንግስትም ሰማያዊ ፓርቲ ከዚህ ኣፍራሽ ድርጊቱ ካልተቆተበ ኣሸባሪ ተብሎ ከነግንቦት ሰባትና መሰል ድርጅቶች ተርታ ሊፈረጅ እንደሚችል ኣስምሮበት ኣልፉዋል ይልቁንም ሰማያዊ ፓርቲ በኣባይ ቦንድ እና በመሰል ጉዳዮች ዙሪያ ኣስተያየት ከመስጠት ታቅቦ፤ ልማታዊ ጉዳዮች ላይ ቢያተኩር በማለት የመንግስት ቃል ኣቀባይ የሆኑት ኣቶ ኣከሌ ተናግረዋል (ኣከሌ ያልኩበት ምክንያት ከመለስ ሞት ወዲህ ሰው ኣጥፊ ብቻ ሳይሆን ኣላፊና ጠፊ እንደህነ ስለተረዳሁ ነው)፤ ኣያይዘውም ሰማያዊ ስሙ ከኦርቶዶክስ ክርስትና እምነት ጋም የተያያዘ ስለሆነ፤ የህገ-መንገስት የበላይነት እና የእምነት እኩልነት በሰፈነበት ሃገር ፓርቲያቸው ኢሃዲግ እንዲህ ኣይነት መድሎ ስለማይቀበል፤ ሰማያዊ በሚለው ላይ ተቀጽላ ጨምሮ (ሰማያዊ ኣል ረካት) ብሎ እንዲያስተካክለው እናሳስባለን፤ ይህ ባይሆን ግን ፤ ህገ መንግስቱ በሚፈቀደው መሰረት፤ ህጋዊ እርምጃ እንደምንወስድ እናሳስባለን። በነገረችን ላይ ይሄ የኣሸባሪነት ህግ ከመጠን በላይ መናፈስ በጀመረበት ዘመን የልጅ ልጃቸውን ማየት የቻሉ ኣያት፤ ልጃቸው እማ ልጄን ማን ልበልው ብላ ለጠየቀቻቸው ጥያቄ መልስ ሲሰጡ፤ ማንስ ብትይው ምን ዋጋ ኣለው፤  ገና ሳይወልድ እኮ ነው መንግስት ስም ያወጣለት፤ ስለዚህ ኣድጎ ግራ ከሚገባው ኣንድ ፊቱን ኣሸብር በይው ኣሉዋት። ኣረ እቴ፦
በነገራችን ላይ የጎጃም ገበሬ ነው ኣሉ፤ ስለ ኣዲሱ የኣደይ ሃዳስ ግድብ  ወይም ህዳሴ ግድብ ከጋዜጠኛ ለቀረበለት ጥያቄ ሲመልስ፤ እናንተ የኢትዮጵያን ባህልና ወግ ለመናድ ስትታገሉ፤ ኣባይ ደሞ የኣማራ ኣፈርን ሲንድ፤ ነው የማወቀው፤ እንግዲህ ዛሬ ኣባይ ከዚህ ጸያፍ ድርጊቱ ታቅቦ፤ እንደ ሴተኛ ኣዳሪ እዚህም እዚያም ከማስካካት እናንተ ባበጃችሁለት ቦይ ለመንዶልዶል መወሰኑ ጥሩ ጅምር ነው፤ ዋናው ቁም ነገር ግን መንግስት ከዚህ ግድብ ምን ይማራል ነው፤ ይህ የሺህ ኣመት ቦዘኔ፤ ጨርቄን ማቄን ሳይል፤ ጉዋዙን ጠቅሎ  እዚሁ የተፈጠረበት ሃገር ለመስተር መሞከሩ፤ መንግስትን ምን ያስተምረዋል፤ የገዛ ሃገራቸውን ኣንጡራ ሃብት ለባ፤ኣዳን የሚቸበችቡ ኣሻጥረኞች ከዚህ ምን ይማራሉ ነው። ብሎ ኣስተያየቱን ሰትቶ ኣልፎዋል።
ሲታረስ ሳያምር ሲታጨድ ሳያምር
ዋራን ኣሳመረው የድንጋይ ቤት ክምር
ያለው ማን ነበር
ሲነገር ሳያምር ሲወራ ሳያምር
ደለል ሻኛ ሆነው የጭቃ ቤት ክምር
ብለን ለኣባይ መሳ ግጥም ገጥመን እንለፋ።
እና ስለ እንቅልፍ ተመልሰን እናውራ….
እናላችሁ  መተኛት ለሚፈልግ ከምግብና መጠጥ ሌላ ሁሉም ይሞዋላለታል። እንኩዋን ሰዉ ዛፍ እንኩዋ እንቅልፍ ለምዱዋል። መወዛወዝ የል፤ ቅርንጫፍ ማፋጨት የለ፤ ዘነበ ኣልዘነብ የለ፤ ከሰው ጉንጭ ውስጥ ገብቶ ለጥ። ማ ወንድ ነው የዘንድሮን ዛፍ የሚቀሰቅሰው። ስሙስ ቢሆን ኣሱም እንደ ቢዮንሴ ሄር ስታይለር …ተቀይሮ። ድሮ ኣባቶቻችን ሰለ ዛፍ ሲያወሩ፤ ዝግባ፤ ዋንዛ፤ ቀርቀሮ፤ ጥድ፤ የባህር ዛፍ፤ ወይራ፤ ኣር ስንቱ፤ የዘንድሮ ዛፍ ለስለስ ያለ ስም ነው ያለው፤ ለስለስ ያለ እጅም ነው የሚይዘው። የዘንድሮ ዛፍ ምንጣፍ ተነጥፎለት ነው ቤት የሚገባው እንጂ በኣህያ ጀርባ ተጭኖም ኣይደል። ከትግራይ ውጭ በኣራቱም ማእዘናት ይበላል፤ ኣወዳይ ወይም በፈረንጅኛው  (I will die) ገለምሶ፤ በለጬ ፤ ጉራጌ ገለመኔ ነው ስሙ። የዚህ የእንቅልፋም  ትውልድ ቀርቀሮና ዝግባ።  ይሄ ትውልድ በእውነትም እንቅልፋም ነው።
ደጉ መንግስቴ በክርስትና ስሙ (የዘመናት ብሶት የወረሰው፤ ወይም የወረረው) (በዳቦ ስሙ ባለ ራእዩ መንግስቴ)…  የኣቡነ ጴጥሮስን ሃውልት ኣፍርሶ (ነቅሎ)፤ ቁልቁል ሲንደረደር በተኛበት ቤቱ የፈረሰበት ሰው ነው ኣሉ እንዴ ይሄ ባቡር ሳይገባ ገጭቶ የጨረሰን ሲገባ ምን ልንሆን ነው ኣለ ኣሉ። ሲገባማ ምን ችግር ኣለው፤ ያባልነት መታወቂያ ከያዝክ እንቅልፍህን ትራንሰፈር ታደርገው ዘንድ በርህ ላይ ቆሜ እየጠበቑ ነው የሚል ኣይመስልሕም።
ባለ ራአይ ስል…. የቀድሞ የሳውዝ ኣፍሪካ ፕሬዝዳንት የሆኑት ኔልሰን ማንዴላን የቀብር ስነ ስርኣት በተሌቪዥን ሲከታተል የነበረ  ኣንድ ታጋይ (በሃደግ)ለማንዴላ እንደኛ ባለ ሯዩ መሪ የጎዳና ተዳዳሪዎችና ሴተኛ ኣዳሪዎች ያላለቁሱለት ለምንድን ነው ኣለ ኣሉ። ስላልወለዳቸው እናም ስላላገባቸው ልበልህ። ምን ልበል እኛ በህግ የተመዘገበ፤  ህገ መንግሱ የሚያውቃት ልጃቸው ቢሊየነሩዋን ሰማኸል መለስን ነበር፤ ታዲያ ጆቢራው ሲሞት ባንዴ (ባሌ ባሌ፥ ኣባቴ ኣባቴ ባዩ መብዛቱ) ድሮም  ሾፌርና የእንትን ወንድ ይሉ ነበር ዘመዶቼ::
ማን ነበር ሎዚች ጦላ ሎጦሞቆ ሴት ሙተኛት ነበር ያለው። ኣይ ሃገር፤ ቡና ቤት ኣረጉሽ፤ ኣይ ትውልድ ቁመን ኣየንሽ።
ሲታረስ ሳያምር ሲታጨድ ሳያምር
ዋራን ኣሳመረው የድንጋይ ቤት ክምር
ያለው ማን ነበር
ሲፈጥረው ሳያምር
ሲገለው ሳያምር
ክፋት ግብር ሆነው የደደቢት ንስር።
ብዬ ለኣባባ መልስ እኔ ወዲ ሃድጊው በጎዳ ልጆች ስም ግጥም ባበረክትስ።
ቸር ይግጠመን

Sunday, December 29, 2013

በከፊቾ ዞን የጽላት ዝርፊያና ቀበኞቹ

http://www.goolgule.com/ethiopian-ark-tabot-looting-in-keficho/

"ባለሃብቶች በእድሳት ስም ቤተ መቅደስ ዘልቀው ጽላት ይቀይራሉ"
tabot
በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች ክልል በከፊቾ ዞን በጥንታዊ አድባራት ጽላት መዘረፉን እናውቃለን ያሉ ለጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ ገለጹ። የዜናው ምንጮች የዞኑ አገረ ስብከት በዞኑ በሚገኙ አድባራት ላይ ምርመራ እንዲያካሂድ ጠይቀዋል። ዝርፊያውን የሚያካሂዱት “ባለሃብቶች” መቀመጫቸውን አዲስ አበባና ጅማ ከተማ ያደረጉ የክልሉ ተወላጆች መሆናቸውን አስታውቀዋል።
ነዋሪነታቸው ቦንጋና ጊምቦ እንደሆነ የሚገልጹት የዜናው ምንጮች “ቀበኞች” በማለት የሚጠሯቸውን የጽላት ዘራፊዎች የዝርፊያ ስልት ተናግረዋል። በመጀመሪያ እድሜ ጠገብ የሆኑትን አድባራት ይለያሉ። በቃፊሮቻቸው አማካይነት መረባቸውን ዘርግተው ሰዎችን ያጠምዳሉ። ህዝበ ክርስቲያን በሚሰበሰብበት ወቅትና ዓመታዊ የበዓላትን ቀን መርጠው በርዳታና በእድሳት ስም ውዳሴ ይቀበላሉ።
በዞኑ የሚገኙት አቢያተ ክርስቲያናት እድሜ ጠገብ በመሆናቸው በርካታ ጥንታዊ ቅርስም እንዳላቸው የሚጠቁሙት ክፍሎች “ያረጁትን አድባራት እናድሳለን በማለት ጥቁር ለምዳቸውን ለብሰው መቅደስ ውስጥ ይዘልቃሉ” በማለት የዝርፊያው ድራማ እንዴት እንደሚከናወን ያስረዳሉ።
ለሃይማኖታቸው የቀኑና የታመኑ የቤተ መቅደስ ጠባቂዎችና አገልጋዮች ሲያጋጥሟቸው መቅደስ ውስጥ ተመላልሰው በሚሰበስቡት መረጃ መሰረት አብረቅራቂ ሃሰተኛ ጽላት በመተካት ዝርፊያ እንደሚካሂዱ፣ ለዝርፊያ የሚመችና ስብናው የወደቀ አገልጋይ ሲያገኙም በግልጽ ያሻቸውን አድርገው ስርቆቱን እንደሚፈጽሙ የዜናው ሰዎች ያስረዳሉ።
ድርጊቱ የቆየና ሰዎቹም የሚታወቁ እንደሆኑ የሚጠቁሙት እነዚሁ ክፍሎች፣ “ቀበኞቹ” ካላቸው የገንዘብ አቅም አንጻር እጃቸው ከወቅቱ ጉልበተኞችና የቤተ ክህነት ከፍተኛ አመራሮች ጋርም የጠበቀ ግንኙነት ሊኖራቸው እንደሚችል ከግምት በላይ አመላክተዋል። በዚህ ተነሳ “እንፈራለን፤ ፊት ለፊት ለመግጠምም እንቸገራለን” በማለት ለጎልጉል የአዲስ አበባ ዘጋቢ ምስጢራቸው እንዲጠበቅ አስጠንቅቀው መረጃውን ለመስጠት ችለዋል።
“ይህንን ዜና ጥቅማቸው የሚነካና ችግር ያለባቸው አካላት ዙሪያ ያሉ ጥቅመኞች ሊያስተባብሉት ይችሉ ይሆናል” ሲሉ ዜናው የሚያስደነግጣቸው ክፍሎች የሚወስዱትን የመጀመሪያ ርምጃ ያመላከቱት ተቆርቋሪዎች፣ “የእኛ ጥያቄ ግን ማጣራትና ምርመራ ተደርጎ ውጤቱ ከታወቀ በኋላ እውነታው እንዲረጋገጥ ነው” ብለዋል።
የዞኑ አገረ ስብከት ዛሬ ነገ ሳይል በተቀደሱ የማምለኪያ አድባራት ላይ የተፈጸመውንና እየተፈጸመ ያለውን ዝርፊያ የማጣራት ሃላፊነት እንዳለበት ያሳሰቡት ክፍሎች፣ ቀበኞቹ በርዳታ ስም እድሳት ባካሄዱባቸው አድባራት ላይ የሙከራ ምርመራ ቢደረግ ጥቆማው ምላሽ እንደሚያገኝም በርግጠኛነት ተናግረዋል።
በእድሳትና በርዳታ ስም መቅደስ በመዝለቅ ከሚከናወነው ዝርፊያ በተለየ በድርድር የሚካሄዱም ዝርፊያዎች ስለመኖራቸው ያመለከቱት ክፍሎች “ጉዳዩ እጅግ ጥንቃቄ የሚፈልግ በመሆኑ ስምና ቦታን ለይተን ለመጠቆም እንቸገራለን” ብለዋል። “መልዕክቱ ለቀበኞቹ፣ ለተባባሪዎቻቸውና የሚሰማ ተቆጣጣሪ አካል ካለ ለነሱ ነው” ሲሉም አክለዋል። በዞኑ ያሉ የህዝብ ወኪል እንደራሴዎችም በዚህ ጉዳይ ላይ ጥንቃቄ ወስደው እንዲሰሩ ጠይቀዋል።
“የቃል ኪዳን ጽላት ዘርፎ ከማነከስና ሰልሎ ከመሞት ውጪ ሌላ ዕድል የለም” ሲሉ ማስጠንቀቂያ ያስተላለፉት ተቆርቋሪ አዛውንቶች በ2005 መገባደጃ ላይ ዋሻ ውስጥ ተገኘ የተባለ ጽላት የት እንደገባ እንደማይታወቅ አመልክተዋል። ዜናው የመገናኛ ሰዎች ዘንድ ሁሉ ደርሶ እንደነበር፣ ነገር ግን በማይታወቅ ሁኔታ ተዳፍኖ መቅረቱ ለጉዳዩ ቅርብ የሆኑ አካላትን እስካሁን እንደሚከነክናቸው አመልክተዋል።
ከዝግጅት ክፍሉ
ይህ ዜና ከመታተሙ በፊት ከጥቆማው በተጨማሪ ሰዎችን ለማነጋገር ተሞክሯል። የዞኑን አገረ ስብከት ለማግኘትም ተሞክሯል። ከዜናው ባህሪ በመነሳት ጉዳዩ ሳይጣራ ግለሰቦችን የሚያመላክቱ መገለጫዎችን ከመጠቀም ተቆጥበናል። በተጠቀሰው ቦታ ብቻ ሳይሆን በመላው አገሪቱ በርካታ ቦታዎች ነዋያትና ጥንታዊ ቅርሶች እንደሚዘረፉና ለዝርፊያው ተባባሪ ሆነው የሚያገለግሉት የድንበር ጠባቂዎች መሆናቸውን በተለያዩ ጊዜያት የሚሰማ እውነት በመሆኑ ተጨማሪ ጥቆማ ለምታቀርቡልን መድረኩ ክፍት ነው። ከቦንጋና አካባቢው፣ እንዲሁም ከጅማ ነዋሪዎች ለደረሰን ጥቆማ እናመሰግናለን። በዜናው ላይ ቅሬታም ሆነ ተቃውሞ ካለ እናስተናግዳለን።

Saturday, December 28, 2013

ልጓሙን የበጠሰው የፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም የስድብ ፈረስ

http://ecadforum.com/Amharic/archives/10508/
December 27, 2013
ከዳኛቸው ቢያድግልኝ
ፕሮፌሰሩ በጽሁፎቻቸው እንዲህ ብለውናል
“…በዓለም ሕዝቦች መሀከል ውድድር ቢደረግ ያለጥርጥር አበሻ አንደኛ ከሚወጣባቸው ነገሮች አንዱ ልመና ሳይሆን አይቀርም፤ ለአበሻ፣ ልመና የኑሮ ዘዴ ነው……”  http://www.goolgule.com/abesha-and-begging-1/
             “…አዳም አበሻ ሳይሆን አይቀርም፤ ሁሉንም ነገር ብላ ከተከለከለው በቀር ብሎ ያስቀመጠው ይመስላል፤ በላባችሁ ወዝ ብሉ ተብለው አዳምና ሔዋን መረገማቸውን አበሻ ገና አልሰማም፤ አበሻ የተፈጠረው ገነት ውስጥ ቁጭ ብለህ ያለውን ሁሉ ብላ በተባለበት ጊዜ ነው፤ እግዚአብሄር አበሻን ሁሉንም ብላ ሲለው ምናልባትም በጆሮው ጭራሽ አታስብ ብሎት ይሆናል …….” (ሰረዝ የተጨመረ)
                 እስከናካቴው “ሆድ” የሚባል ቃል ከአበሻ ቋንቋ ፈጽሞ ቢሰረዝ ቋንቋው ብቻ ሳይሆን አበሻም ጉድ ይፈላበታል።  አዕምሮ ፣ ሕሊና የሚባሉትን ቃላት አበሻ አያውቃቸውም፤ ተግባራቸውንም ሁሉ ለሆድ ሰጥቶታል።   (ሰረዝ የተጨመረ) http://www.zehabesha.com/amharic/archives/9015
ልጻፍ ልተው… ምናልባት… እንዲያው ምናልባት በዚሁ የሚያበቁ ከሆኑ አይቶ እንዳላየ ማለፍ ይሻል ይሆናል ስል ልጓሙን የበጠሰው የስድብ ፈረሳቸው በማንአለብኝነት ጋለበብን። ባእዳን አበሽ እያሉና እየሰደቡ ይገድሉናል። የራሳቸው ታሪክ በረሀብ ቸነፈርና ስደት የተሞላ እንዳልሆነ ሁሉ በመዝገበቃላታቸው ውስጥ ኢትዮጵያን የረሀብ ምልክት አድረገው የሚያዋርዱን በርካታዎች ናቸው። ፕሮፌሰሩ በአንድ ወቅት ሲሉ እንደሰማሁዋቸው  ወያኔዎች ከዱር ወደከተማ ሲገቡ ህዝቡን ፈሪ ለማድረግና የሚያከብረው ምልክት ለማሳጣት በየቀዬው በህብረተሰቡ ዘንድ የሚከበሩትን እያፈላለጉ በአደባባይ ፂማቸውን ይዘው በመጎተት ያዋርዱዋቸው ነበር። ይህን መሰሉ የወያኔዎች ተግባር በሚያሳዝን ሁኔታ በፕሮፌሰሩም ላይ በተደጋጋሚ ደርሶባቸዋል። የወያኔዎች ኢትዮጵያዊነትንና ኢትዮጵያን የማዋረድ ዘመቻ ዛሬም እንደቀጠለ ነው። ታዲያ ይህ ባለበት ሁኔታ የእውቀት ጣርያ ላይ ደርሰዋል የሚባሉት አዛውንቱ ፕሮፌሰር መስፍንም  በአሮጌና ያለአግባብ በተደረደረ ምሳሌ ይህን መከራ የበዛበትን ህዝባችንን በሚሸነቁጥ የጅምላ ስድብ መቀጥቀጣቸው ግር የሚያሰኝ ሆነብኝ። ይህ ወቅትና ሁኔታን ያላገናዘበ መፍትሄ የመጠቆም፣ የማስተማር አቅምም የሌለው ኢትዮጵያዊነትን የሚያዋርድ ጅምላ ስድብና ሽሙጥ በተከታታይ ሲወርድብን አይቶ እንዳላየ ማለፉ ክብራችንን ለማጉደፍና ለማዋረድ ኢትዮጵያችንን ለማንቋሸሽ ለሚተጉት ዱላ ማቀበል ይሆናል። እናም ይህ ጥያቄ ይከነክነኝ ገባ። እውን አበሻ ሥራ ጠል፣ ለማኝና ሆዳም ነውን? በምን ጥናት በማንስ ትንታኔ?
Prof. Mesfin Woldemariam : is an Ethiopian Human Rights activist and philosopher
እድሜአቸውን ሙሉ ሀገራችንን አገልግለዋል ሲባል መስማቴ ብቻ ሳይሆን በባህላችን አዛውንት ይከበራልና  ክብራቸውን የሚያጎድፍ  ትችት ማቅረብ አልፈልግም።  ቢሆንም ታድያ የሰሞኑ ማቆሚያ ያጣው የስድብ ጅራፍ ዘላቂ ጉዳቱ ከፍተኛ ነውና አክብሮቴን ሳላጎድል እባክዎን የስድብ ፈረስዎን ልጓም ያዝ አድርጉልን እላለሁ።
በሀገራችን አዋቂ ነን የሚሉ ሰዎች  ከነሱ የተለየ ሃሳብ ይዞ የሚመጣን ተወያይቶ የተሻለውን ሃሳብ ከመደገፍ ይልቅ ለየት ያለ ሃሳብ ያቀረበውን አንገት የሚያስደፋ የስድብ ናዳ ማውረድ ይቀላቸዋል። ይህንን በመፍራት አዋቂዎቹ ግዙፍ ስህተት ሲፈጽሙ በዝምታ ማለፍ ለሌላ  ስህተት በር መክፈት ይሆናል። አንዳንድ ሰዎች ደግሞ ጽሁፍን በይዞታው ሳይሆን በጸሃፊው ማንነት እየመዘኑ ጸሀፊው በግልጽ ያስቀመጠውን ሃሳብ ወደጎን ትተው  ያልተባለውን መልካም ሃሳብ ፍለጋ እየማሰኑ የራሳቸውን ትርጓሜ ይሰጣሉ። ሰአሊ በስህተት የረጨውን ቀለም “አብስትራክት” ነው ብለው በምናባቸው ውብ ስዕል እንደሚሰሩት አይነት ከስድብ ጀርባ ሙገሳ መፈለጉ ከንቱ  ነው።
የፕሮፌሰር ተከታታይ ጽሁፎች የተጻፉት ኢትዮጵያን በስፋት በማያውቅ ሰው፣ ሀሳብን ለህዝብ ለማቅረብ ምን አይነት ጥንቃቄ የተመላበት የምርምር ጥበብ አስፈላጊ እንደሆነ በማያውቅ ሰው ቢሆን፣ ሀሳብን የማስፈር ዓላማና ግብን መረዳት በማይችል የእውቀት አድማሱ ያልሰፋ፣ በሌሎች ሀገራት የሚኖሩ ሰዎችን አኗኗር በተመለከተ ምንም ግንዛቤ በሌለው ሰው ወይም እንዲያው ለፌዘኛ የመሸታ ቤት ቀልድ ሲባል ለተወሰኑ ታዳሚዎች የቀረበ ቢሆን ምንም  ትኩረት መስጠት ባላስፈለገ ነበር።  ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም ግን አለምን ተዘዋውረው የጎበኙና ያልኖሩበትን ዘመንና ያልጎበኙትን አገር ህዝብ አኗኗር በምርምርና በንባብ ጠንቅቀው የተረዱ እድሜ የጠገቡ ምሁር ናቸውና በምንም ጥናታዊ መረጃ ባልተደገፈ መንገድ የአንድን ጥንታዊና ታሪካዊ ሀገር ሕዝብ በዚህ መልኩ ማሳነስና ከሌላ ፕላኔት የመጣ ሰንካላ ፍጡር ማስመሰል እድሜያቸውንና እውቀታቸውን አይመጥነውም። የአንድ ሀገር 90 ሚሊየን ሕዝብ በአንድ ቅንፍ ውስጥ “አበሻ” ብለው ከተው እንኳን የሰው ልጅ ቀርቶ ማንኛውም ማህበራዊ እንስሳ የሚያደርገውን ተሳስቦ፣ ተዛዝኖ፣ ተካፍሎ መኖርን በዚህ መልክ አሳንሶ ኢትዮጵያዊነትን ማዋረድ ታላቅ ስህተት ነው።
ኢትዮጵያዊነትን እያዋረዱ አገር አልባ ሊያደርጉን አዲስ ታሪክ ሊጽፉልን ያሰፈሰፉ ጠላቶች አራት ኪሎ በተቀመጡበት ሰዓት፤ ከልመና ግርድና ይሻላል ብለው የፕሮፌሰሩ የልጅ ልጆች በመላው አለም ተበትነው ለራሳቸውና ለቤተሰባቸው ቢያልፍልን  ብለው በሰው ሀገር እየተደፈሩ፣ እየተዋረዱ በሚዳክሩበት በዚህ ዘመን፣ በርካታ እናቶች አራስ ልጆቻቸውን ታቅፈው ትንሽ ሳንቲም ለማግኘት በየመንገዱ ዳር ጥቂት የተቀቀለ ድንችና ንፍሮ ለመሸጥ ጸሀይና ብርድ ሲፈራረቅባቸው ውሎ በሚመሽበት ዘመን፣ ደካማ እናቶች ወገባቸው እስኪጎብጥ ቅጠልና ጭራጭሮ ተሸክመው የእለት ጉርሳቸውን በሚያገኙበት ሀገር፣ ተራራ የሚያክል ሸቀጥ በጭንቅላታቸው ተሸክመው የሚሮጡ ወገኖች በሚርመሰመሱበት ሀገር፣ ህጻን አዛውንቱ ትንሽ ባገኝ ብሎ ሊስትሮና ማስቲካ ነጋዴ በሆነበት ሀገር ፕሮፌሰሩ ኢትዮጵያውያን ሥራ-ጠል ሆዳምና ለማኝ መሆናችንን አስረግጠው ሲነግሩን  መስማት እጅጉን ያማል።
ሀገር በሞታቸው ያቆዩልን ተዋርደው አጽማቸው ከመቃብር ሀውልታቸው ከቆመበት እየፈረሰ ባለበት፣ የኢትዮጵያን ገጽታ ማቆሸሽ የመንግስት ፖሊሲ በሆነበትና ግፈኞችና ጎጠኞች ሰው በሀገሩ ሰርቶ ሰው መሆን እንዳይችል በየማዕዘናቱ እየበተኑት ባሉበት የመከራ ጊዜ የኛው የተማሩ አዛውንት ዋናው ተሳዳቢ መሆናቸው ያሳዝናል። አብረን ስለበላን ሆዳም፣ ተቸግሬአለሁ ብሎ ድጋፍ ለጠየቀ ወገን ስለለገስን ኅሊና ቢሶች አሉን። ሰውን ከመዝረፍ መለመንን ስለመረጠ ፈሪና ጅል፣ ስላመነ ሞኝና ተላላ አድርጎ መመልከት ነውር ነው። ይህ መተዛዘንና ተካፍሎ መብላት ቀለም ያልቆጠረው ኢትዮጵያዊ ያቆመውን መሰረትና  ያቆየውን ባህላዊ እሴት ልናከብረውና ልንከባከበው ይገባል።  በተከታታይ በፕሮፌሰሩ የተጻፉት ጽሁፎች የሚደመድሙት አበሻ ስራ ጠል መሆኑን፣ ሆዳምነቱንና፣ ለማኝነቱን ነው። በሚቀጥለው ጽሁፋቸው ደግሞ ሌላም ሊያስከብሩን የሚገባቸውን ባህሪያችንን ልናፍርባቸው የሚገቡ አጉል ገጽታዎች አድርገው ይጽፉልን ይሆናል። ይህ ወይ እራስን ከፍ ከፍ ለማድረግ ሌላውን ዝቅ ዝቅ ማድረግ በመፈለግ አለዚያም ተስፋ የቆረጠ ሰው አገርን በጅምላው ሊያስነውር የሚያደርገው ድርጊት ይመስላል።
ለመሆኑ ፕሮፌሰሩ ሆድ መውደድን እንዴት ይገልጹታል? ምግብ መውደድ፣ መውደድ ብቻ አይደለም አጣፍጦና አስውቦ መብላት አንደምንስ ያስወቅሳል? በውጪው አለም የምግብ ስራ ጥበብ ምንኛ የተከበረ ሙያ መሆኑን፣ ቴሌቪዥኑ በሙሉ በምግብ ስራ ፕሮግራም መጨናነቁንና የምግብ ስራ ጥበብ መጻህፍት ጸሀፊዎች ምንኛ የተከበሩ መሆናቸውን እንዴት ዘነጉት? ምግብ እኮ የህልውና መሰረት ነው በአካል ለመዳበር፣ አእምሮን ለማጎልበት፣ የማስታወስና የማሰብ አቅምን ከፍ ለማድረግ የታመቀውን የተፈጥሮ አቅም ለማውጣት የሚያግዝ ነው። በጣም የሚገርመው ደግሞ ቢወደውም ጥቅሙን ቢረዳውም እንኳ አልሚ ምግብ አግኝቶ ሳይሆን በተገኘው ምግብ ሆዱን ሞልቶ የሚያድር እንኳን በሌለበት ሀገር ውስጥ ለሚገኝ ሕዝብ በረሀቡ ላይ ሆዳም የሚል የስድብ ምርቃት ማከሉ አሳዛኝ ነገር ነው። ምክርም ይሁን ግልጽ ዓላማ የሌላቸው ጽሁፎች መጻፉ ግቡ ኢትዮጵያን ለሚያዋርዱት ‘ምሁራዊ’ ድጋፍ መስጠት ብቻ ይመስለኛል።
በምግብ አብዝቶ መብላትና ሲያመነዥጉ በመዋል የሚታወቁት የሌሎች አገሮች ዜጎች ናቸው።  ይህንን የማያውቅ ከመንደሩ አለፍ ብሎ የማየት እድል ያልገጠመው ሰው እንጂ እንደ ፕሮፌሰር አውሮፓ ኤዥያና ሰሜን አሜሪካን ያሰሰ ሊሆን አይችልም። ለዚያውም ባንድ ወገን ሆዳምና አይነቱና ብዛቱ ወደር የማይገኝለት ምግብ ስለመብላቱ የሚነገርለት ሕዝብ በሌላው የፕሮፌሰሩ ፅሁፍ ለማኝነቱንና አምላክ ደድብ ያለው ሥራ-ጠልነቱ ይበሰርለታል። አንዱን ፅሁፋቸውን ከሌላኛው ማገናኛ ድልድዩ ምን ይሆን ያሰኛል። ለማኝ እኮ አጣጥሞና አማርጦ ለመብላት ያልታደለ ምርጫ አጥ ነው። ሥራ ጠልቶና ለምኖ አማርጦ መብላት ከተቻለማ ኢትዮጵያችን መና ከሰማይ የሚዘንብባት ሁናለች ማለት ነው።
ኢትዮጵያዊም ሆነ ሌላው በገበታ ዙሪያ የሚሰባሰበው ለመብላት ምክንያት በመፈለግ አይደለም፤ ምግቡ የመገናኛው ማጣፈጫ እንጂ። ሰርግም ሆነ መልስ፣ ልደትም ሆነ ተዝካር፣ ፋሲካም ሆነ እንቁጣጣሽ በጋራ ገበታ መቀመጥ መሰረታዊ ምክንያቶቹ ማህበራዊ ግንኙነቶች ናቸው። የሰው ልጅ ማህበራዊ እንስሳ ነው። አብሮነቱን ካላዳበረ ተነጣጥሎ ይሞታልና የትኛውም ማህበረሰብ በየትኛውም የዓለም ጫፍ ቢኖር በራሱ መንገድ ይሰባሰባል። አብሮ ያድናል፣ ተጋግዞ ያርሳል፣ ፈረቃ ገብቶ ያመርታል። ያንን ውበት ለመስጠትና አብሮነቱን ለማሳመር ደግሞ በጋራ ገበታ ይቁዋደሳል። ታዲያ ለምንድን ነው ኢትዮጵያውያን አብረው መብላታቸው ልዩ እንከን ተደርጎ የሚቀርበው? እንዲያውም ኢትዮጵያውያንን ሰብስቦ የያዘው ጠንካራ ድር ቢኖር እንዲህ ያለው በደስታና በሀዘን አብሮ መሆኑ ነው።  አብሮ ያቆመን ሲወርድ ሲዋረድ የመጣው ባህላዊ እሴት እንደ ሁዋላ ቀርነትና ሆዳምነት ሲቆጠር ስቆ ማለፉ የሚያስከትለውን እራስን የማዋረድን ጣጣ ልብ ያለማለት ነው። ኢትዮጵያውያን ለዘመናት የቆዩ በአብዛኛው ከሀይማኖት ጋር የተገናኙ አሰባሳቢና አገናኝ በዐላት አሏቸው። በለጸጉ የሚባሉት አገሮች ደግሞ ከሀይማኖታዊ በአላት በተጨማሪ ለንግድ የሚመቹ አዳዲስ በዐላት እየፈጠሩ  አብሮነታቸውን የሚያጠናክሩበትን መንገድ ፈጥረዋል።  የእናት ቀን፣ የአባት ቀን፣ የፍቅር ቀን፣ የምስጋና ቀን እያሉ አብረው ይበላሉ ይጠጣሉ። ስለዚህም ኢትዮጵያውያንን አብረው በመብላታቸው ሆዳም የሚላቸው በርዕሰ ጉዳዩ  ላይ ትንሽም ቢሆን ጥናት ያላደረገ ብቻ ነው።
ከዚህ ቀደም እንደ ጻፍኩት ኢትዮጵያውያንን ‘አበሻ’ ባልል እመርጣለሁ ምክንያቱም ኢትዮጵያ የሚለውን ስም ለማሳነስ በርካቶች አበሻ የሚል ስያሜ ላይ በመንጠልጠል መጥፎና ደካማ የሆነውን ነገር ሲያጎሉ ማየት እየበዛ ነው። ‘አበሽ’ የሚለውን የንቀት መሰል አጠራር የሚጠቀሙትም እነማን እንደሆኑ እናውቃለንና ኢትዮጵያ እያልኩ እቀጥላለሁ። እናም ክቡር ፕሮፌሰር የአለም ሕዝብ ከእንቅልፉ ተነስቶ ማዛጋት ሲጀምር ነቃ የሚያደርገውን ቡና…. ፓስታና ማኮሮኒ እያማረጠ የሚበላበትን ስንዴ…. ‘ግሉቲን’ ሆዱን እየነፋው ፊቱን እያዠጎረጎረ የሚያስቸግረውን ሕዝብ ጤናማ የሆነ እሹኝ ፈትጉኝ የማይለውን ጤፍ ጠገብ ሲል ደግሞ የበላውን የሚያወራርድበትን ጥሙን የሚያስታግስበትን ገብስ ለአለም ያበረከተው “ሰነፍ፣ ሆዳምና ለማኝ” እየተባለ የሚዘለፈው የኢትዮጵያ ገበሬ ነው። የሀገሬ ገበሬ ጀምበር ወጥታ እስክትጠልቅ ድረስ የሚተጋ ጠዋት ያሟሸውን አፉን ማታ ባገኛት እፍኝ እህል እየዘጋ የሚኖር ነው። ይህ ደግሞ ከሰማንያ በመቶ በላይ ኢትዮጵያውያንን ይወክላል። ይህ ወገንዎ ክብር እንጂ ስድብ፣ ሙገሳ እንጂ ውርደት አይገባውም። በምንም መልኩ ኢትዮጵያውያንን እርሶንም ጨምሮ እግዜር በጆሮአችንን አታስቡ ብሎ መርጦ አላደደበንም። ያንን ስድብ ተቀብለው የሚኖሩ ደደቦች ካሉ ምህረቱን ያውርድላቸው። ሀገራችንን ለማጥፋት የሚያዋርዱን በቂ ጠላቶች አሉንና እራሳችንን በማዋረድ ለጠላት ስራውን አናቅልለት።
ኢትዮጵያውያንን ከሀገራቸው ውጪ የሚያሳዩትን የስራ ፍላጎትና መነሳሳት ለመመልከት እድል ላገኙ ሁሉ ኢትዮጵያውያን ሀገሬውንም ሆነ ሌሎቹን መጤዎች በልጠው ሲተጉና ውጤትም ሲያመጡ እንጂ ሰነፍ በመሆን ከሌላው አንሰው አያዩም። ስለዚህ በጅምላ ኢትዮጵያውያንን ስራጠል ሰነፍ አድርጎ መኮነኑ ውሃ አያነሳም። ኢትዮጵያውያን ስራጠል ከሆኑ በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ወጣቶች ስለምን ወደ አረብ አገር ሊሄዱ ቻሉ? ለልመና ነበር? ለመሆኑ ኢትዮጵያውያን በተሰደዱባቸው ሀገራት በአውሮፓና አሜሪካ በአፍሪካ ሀገራትም እንኳን የሚታወቁት በስራ አይደለምን? ባዶ እጃቸውን ከሀገር ወጥተው አዲስ ሀገር ውስጥ ኑሮ መስርተው ከብረው ለመኖር የቻሉት በአስማት ነውን? ስለዚህ ፕሮፌሰሩ እነዚህ በአንዲት ጀንበር ዘርፈው የከበሩ ነጣቂዎችን መንግስት ብለው መንግስት አንደተቀበለው ቻይና እንዳረጋገጠው ብለው ስንፍናችንን ሲደመድሙ የፌዘኛ እንጂ ምሁራዊ ትችት አይመስልም። አንድን በይሉኝታና በፈሪሃ እግዚአብሄር (አምላክ) የሚኖርን  ሕዝብ አዕምሮና ሕሊና ቢስ የሚል ሰው እውን ሕሊናና አእምሮ አለው ብሎ መገመትስ ይቻላልን?
ኢትዮጵያውያንስ እንዴት ሁኖ ነው በሆዳቸው ነው የሚታወቁት የተባለው? ኢትዮጵያውያን ተጋብዘው ድግስ እንኳን ሲሄዱ “ቤታቸው ምግብ የለም እንዴ” ላለመባል እቤታቸው በልተው የሚሄዱ ናቸው። ነፃ ምግብ አለ ሲባሉ ለሳምንት የሚበቃ ቀለብ በሆዳቸው ለመጫን የሚዳዳቸው ሌሎች አንጂ ኢትዮጵያውያን አይደሉም። ኢትዮጵያዊውማ ከሆዴ ይልቅ ክብሬ በማለት እርቦትም አሁን በላሁ ነው የሚለው።
ሰዎች ይህንን ስራ ከምሰራ ለምኜ እበላለሁ የሚሉበት ዘመንም ከነበረ በትንሹ ግማሽ ምዕተ አመትን አሳልፏል። ይህም ክስ እውነት እንኩዋን ቢሆን ኢትዮጵያውያንን ለይቶ ከንቱና ርካሽ የሚያደርግበት ምንም ሚዛን የለም። በየትኛውም የአለም ክፍል ቢሆን በአንድ ወቅት የተናቀ ስራ ነበር። ዛሬም ቢሆን ይህን ከምሰራ ዌልፌር ምን አለኝ ብሎ እጁን አጣጥፎ የሚቀመጥ ስንት ፈረንጅ በየሀገሩ አለ። ሌላም አንድ እውነት አለ፣ ሰዎች ከልምዳቸው ውጪ የሚመጣን ነገር የመቀበል ፍላጎታቸው ውሱን ነው። ለምሳሌ ከብት አርቢዎች እርሻን በንቀት ይመለከታሉ። አንዳንድ ከብት አርቢዎች ለምን እነደዚህ ያለ ስራ አትሰሩም የሚባል ከአካባቢው ሁኔታ ጋር የተያያዘ ጥያቄ ሲቀርብላቸው የኛ ዘሮች ይህንን አይሰሩም ይህን የሚሰሩት ሌሎች ናቸው ይላሉ። አንጥረኞች፣ አዝማሪዎች፣ ነጋዴዎች ሁሉም የለመደውን ስራ አጥብቆ መያዝ የኢትዮጵያውያን ብቻ ባህሪይ አይደለም። እንዲያም ሆኖ ኢንጅነሮች፣ የሙዚቃ ጠበብቶች፣ ዶክተሮች የመንግስት ተጡዋሪ ላለመሆንና ለቤተሰባቸው የተሻለ ህይወት ለመስጠት ስራ ሳይንቁ ከጠዋት እስከማታ መኪና በመጠበቅ፣ ታክሲ በመንዳት፣ ዘበኛ በመሆን፣ ጽዳት ሰራተኛ በመሆን ይዳክራሉ። እንዴት ነው ይህን ህዝብ ስራጠል አድርጎ መኮነን የተቻለው?
በሀገራችን ያለጥናትና በቂ መረጃ በምሁሩ ምክር የሰው ንብረት መውረስና ማህበራዊም ሆነ ኢኮኖሚያዊ ጥፋት በስመ ሶሻሊዝም በተፈጸመበት ጊዜ የተመለከትነው አንድ እውነት አለ። ሁለት ስራ መስራት አድሃሪነት ነበር ገንዘብ መያዝና ፈጠራ ወንጀል ነበር። ሶሻሊዝምን ያመጣውና መስራትንና መክበርን ወንጀል ያደረገው ተማርኩ ያለው ወገን የመረጠው የሶሻሊዝም መንገድ ነበር። እንዲያም ሆኖ በአዋጅ ሰዎች ድህነትን እንዲቀበሉ በተደረገበት ጊዜ እንደ አቅምቲ ከበርቴ ተብለው ሀብት ንብረታቸው እየተዘረፈ ሰዎች ወደ እስርቤት በተጋዙበት ጊዜ አዲስ አበባ የተከፈቱ ምግብ ቤቶች (ኢድዩ ቤቶች)፣ ባልትና ቤቶች ሁሉ ሕዝባችን ችግሩን ለማሸነፍ ምን ያህል የሚፍጨረጨር እንደነበረ የሚያስመሰክር ታሪካዊ ወቅት ነበር። እነዚያ “እመቤቶችና ወይዛዝርቶች” ሆቴል ቤት ከፍቼ ለማንም ከማስተናግድ ልመና እመርጣለሁ አላሉም።
ኢትዮጵያውያኖች ለማኞች መሆናችንን ፕሮፌሰር በተለያየ ምሳሌም አስቀምጠዋል። መንግስትን መጠየቅን፣ ሰውን መማለድን (ድርድርን)፣ ትህትናንና ሰላማዊነትን ፕሮፌሰር በልመናነት መድበውታል። እውነታው ግን እነኚህ ባህሪያት አስተዋይነትንና ህግ አክባሪነትን ነው የሚያመለክቱት። ሁሉንም በጉልበት የሚያስፈጽም ማህበረሰብ በሰላም መኖርም አይችልም። በርካታ ታጋዮች የኔ መንገድ ብቻ ነው ትክክል በማለት የተለየ አመለካከት ባሳየው ላይ ተከታታይ በደልን በመፈጸማቸው ሰዉ ክፉኛ እንዲሸማቀቅ ተደርጎአል። ነገርግን ሕዝቡ የለማኝ ባህሪ ተጠናውቶታል ብሎ መደምደም ከባድ ስህተት ነው። ፕሮፌሰር ደግሞ ሰላማዊ ትግል ብቻ የሚሉ እንደመሆናቸው መጠን ዘራፍ ብሎ ለዱላ ከመጋበዝ ይልቅ መንግስትን በጥሞና መማለድን የሚደግፉ ኢንጂ እንዴት የሚኮንኑ ሊሆኑ ይቻላቸዋል?
የመጽዋችና የተመጽዋች ግንኙነት ያለው ደግሞ በኢትዮጵያ ብቻ አይደለም። ምክንያቱም ያለውና የሌለው በየሀገሩ ነው ያለው። ያለው ደግሞ ለተቸገረው መቸርን የማያውቅ ከሆነ በሰላም ወጥቶ መግባትም አይቻልም። ከመለመን ይልቅ በጉልበት ቀምተው የሚወስዱ ነጣቂዎች የበረከቱበት ሀገር ይሻላል የምንል ካለን የማሰብ አቅማችን ተናግቶአል ማለት ነው።  ኢትዮጵያውያን ካላቸው ላይ ቀንሰው ለሌላው መስጠታቸው የስነምግባርና የሞራል ባለጸጋ መሆናቸውን ያመለክታል እንጂ ልመናን የሚያበረታቱ ሰነፍ ማምረቻዎች አያሰኛቸውም። ጧሪ ያጡ አዛውንቶች፣ የአካል ጉዳተኞችና ህመምተኞች በመሆናቸው ስራ ማግኘት የማይችሉና ጤነኛም ሆነው ስራ ማግኘት ያልቻሉ መለመን ሊገደዱ ይችላሉ። ይህ ሰነፍ አያስብላቸውም። ባደጉት ሀገራትም የ ‘ዌልፌር/ድጎማ’ አሰራር አላቸውና ድጋፍ ለሚሹ ወገኖች የተለያዩ እርዳታዎችን ይለግሳሉ። ይህ መንግስታዊ ድጋፍ በሌለባት ኢትዮጵያ ወገን ወገኑን መርዳቱ አስፈላጊና የሚደነቅ እንጂ የሚያስወቅስ አይደለም። ኢትዮጵያውያን ይህንን የመረዳዳት ባህል ባያሳድጉ ኖሮ የኢትዮጵያ የመከላከያ ሰራዊት በተበተነ ጊዜ መሳርያውን ተሸክሞ ሰለ እግዚአብሄር ውሀ ስጡኝ ብሎ ባልጠየቀ ነበር። ተደራጅቶ መዝረፍ ሲችል ወርቅ ቤት ተደግፎ የሚለምን በዲሲፕሊን የታነጸ ጦር ኢትዮጵያ ብቻ በመኖሩ ጨዋና ህግ አክባሪ ያደረገንን ባህል ልናመሰግን ይገባል። ከዚህም ባሻገር  ‘ልመና’ የሌለበት አገር የለም። አሜሪካም ሆነ አውሮፓ ወይም ኤዥያ በውበቱ ከሚያፈዝ ህንጻ ስር  ቆቡን ዘርግቶም የሚለምን ሆነ ፕሮፌሰር እንደጠቅሱት የድሬዳዋ ለማኝ ብር ስጠኝ እያለ እንደማዘዝ የሚያደርገው ለማኝ ሞልቶዋል።
ልመናና ጸሎት ተመሳሳይ ትርጉም ከተሰጣቸው ደግሞ ሁሉም አገሮች ውስጥ ጸሎት አለና ልመናው አለምን አስጨንቆአል ማለት ነው።  ድርድርም ልመና ከተባለ በትህትና የቀረቡ ጥያቄዎች ሁሉ ልመና ይደረጋሉና ጨዋነት እንደክፉ ባህሪ ሊታይ ነው ማለት ነው። ላሊበላነትም የልመና መስክ ሆኖ ተተችቷል። ነገር ግን ዘፋኝ ሲዲ አሳትሞ ለገበያ ሲያቀርብ ለማኝ አንለውም። አዝማሪዎችና ላሊበላዎች ደግሞ ዛሬ ላለው ኪነታዊ ጥበብ መሰረቶች ናቸው። ስለምን የቀድሞውን ነገር ሁዋላ ቀርና እርባና ቢስ እንደምናደርግ አይገባኝም።
የቆሎ ተማሪ በልመና ስለተለከፈ አይደለም የሚቀፍፈው። የሀገሬ ባላገርም የትምህርትን አስፈላገነት ስለተረዳ ካለችው ቆንጥሮ ያካፍላቸዋል።  ፕሮፌሰርም ሲማሩ የተሰጣቸው መማርያ፣ የጠጡት ወተትና  ልብሳቸውን ያጠቡበት ሳሙና እንደ ቆሎ ተማሪዎች ሰለ ማርያም ብለው ቆዳ ለብሰው ቀፈፋ ባይዞሩም ያው ከንጉሱና ከህዝቡ ቀፈፋ ነበር። እኛ ካልቻልንበት ያልቻልነውን በመጠቆም ማሻሻል እንጂ ያለፈው ትውልድ በቻለውና ባወቀበት መንገድ ሰርቶ ያቆመልንን  አገር ማዋረድ ወንጀል ነው።
ኢትዮጵያ እንደ ሀገር የቆመችው ባሉን ማህበራዊና ባህላዊ እሴቶቻችን ነው። የድሮውን አሳድጎ ዘመናዊ ማድረግ ወይም የተኮረጀውን ከሀገር አስማምቶ ጥቅም ላይ ማዋል ስላቃተን የነበረውን ስንወነጅል ልንኖር አይገባም። አገርን በጅምላ ስንወነጅል ራሳችን የምናበረክተውን እንገምግም። ራስን እያዋረዱ ክብር መሻት ሞኝነት ነው። ከልመና ለመውጣትና ገበና ለመሸፈን አስፈላጊ የሆኑ ተቋማት እንዲፈጠሩ ማበረታት ያሉትንም ማጠናከር እንጂ ወገን በሀዘኔታ ካለችው ላይ ስለሰጠ የተቸገረም ስለለመነ ማውገዙና በሽሙጥ መውገር ምን ይረባናል? ማንም በእርግጠኛነት ሊናገር የሚችለው ኢትዮጵያውያን ለማኝ፣ ሆዳምና ሥራ-ጠል ሳይሆኑ ዘመናትን የሚሻገር ባህልን ያሳደጉ ሲቸገሩ ተረዳድተው ሲመቻቸው አብረው ተደስተው የሚያኖራቸውን ባህል ያቆዩ ታታሪ ሰራተኞችና የሚረዳዱ መሆናቸውን ነው። የእውቀት መነጽራችን ይህንን ላላስመለከተን መቃወምና መንቀፍ ብቻ የእውቀት ምልክት የሚመስለን ህዝብን ከመስደቡ ብንታቀብና  የማስተዋል አቅማችንን ብናዳብረው ይበጃል።
ሀገር አዋራጅ መሰረተቢስና ውልየለሽ ጅምላ ስድብን እውነት ነው ብሎ መቀበል ተቀብሎም ስድቡ ይገባናል በማለት እየተቀባበሉ መሰዳደብ ትክክል አይደለም። ስለዚህም በተከበሩ ፕሮፌሰር ስለተጻፈ ብቻ እንደታላቅ ግኝት በየሚዲያው ማሰራጨቱም “ሞኝን አንዴ ስደበው እራሱን ሲሰድብ ይኖራል” የሚለውን ብሂል በተግባር ማዋል ይሆናል። ኢትዮጵያንና በልጆቿ እየተሸረሸረ ያለውን ኢትዮጵያዊነትን እናድን ዘንድ እንትጋ።

Friday, December 27, 2013

ትግሉ የሁሉንም ተሳትፎ የሚጠይቅበት ወሳኝ ምእራፍ ላይ ደርሷል


ራሱን የብሄረ አማራ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን) ብሎ የሚጠራው ድርጅት በከፍተኛ የፖለቲካ ኪሳራ ውስጥ ገብቷል። የህወሃትን ዙፋን ከመጠበቅ ባለፈ ምንም ሚና የሌላቸው የብአዴን አመራሮች ያለፉትን ሶስት ወራት በተለያዩ መንገዶች የድርጅቱን አባሎች ሲገመግም ከርመዋል። በግምገማዎች ላይ እንደተረጋገጠው ብአዴን የህወሀትን ዙፋን ሊሸከሙ የሚችሉ ወጣቶችን ኮትኩቶ ለማሳደግ አለመቻሉ ነው። በብአዴን ውስጥ ለሚታየው የውስጥ ትርምስ በድርጅቱ ውስጥ የሚገኙ የግንቦት7 አባላትና ደጋፊዎች እየተጫወቱት ያለው ሚና በሌሎች ድርጅቶች ውስጥ ላሉ የንቅናቄው አባላት ጥሩ ትምህርት የሚሰጥ ነው። የንቅናቄው አባሎችና ደጋፊዎች በድርጅቱ ውስጥ የታቀፉ ወጣቶችን የፖለቲካ ግንዛቤ ከማሳደግ ጀምሮ ፣ የንቅናቄውን መረብ እስከ ወረዳዎች በመዘርጋት ከፍተኛ ሚና በመጫወት ላይ ናቸው። ሰሞኑን በገሀድ በየግምገማዎች ላይ ሲነገር እንደነበረው ብአዴን እወክለዋለሁ ከሚለው የአማራ ህዝብ ሙሉ በሙሉ ተነጥሎ በአየር ላይ የተነሳፈፈ ድርጅት ሆኗል።
ይህን እውነታ ዘግይተው የተረዱት የብአዴን ዙፋን ጠባቂ አመራሮች የሚይዙትን የሚጨብጡትን በማጣት የተለያዩ ውሳኔዎችን እያሳለፉ ነው። ታማኝ የሚሉዋቸውን ካድሬዎች በየወረዳዎች በመላክ በግንቦት7 የሚጠረጠሩትን ወይም የግንቦት7 አባሎች ናቸው ተብለው ከሚገመቱ ሰዎች ጋር በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ግንኙነት አላቸው ተብሎ የሚታሰቡትን ሰዎች በመያዝና በማሰቃየት ሌላው ወጣት ንቅናቄውን እንዳይቀላቀል ለማድረግ እቅድ ነድፈው ለመንቀሳቀስ አስበዋል። እንዲሁም አንድ ለአምስት የተባለውን አደረጃጀት በመስሪያ ቤቶች፣ በቤተሰብ፣ በትምህርት ቤቶችና በተለያዩ ተቋማት ላይ በስፋት በማውረድ፣ የሰውን የእለት ተእለት እንቅስቃሴ ለመቆጣጠር አልመዋል። ወጣቱ አካባቢውን እየለቀቀ ግንቦት7ን ለመቀላቀል የሚያደርገውን እንቅስቃሴ የአካባቢ ፖሊሶችንና የድንበር ጠባቂዎችን በማጠናከር ለመቆጣጠር ውሳኔ አሳልፈዋል።
በድርጅቱ ውስጥ የግንቦት7 ደጋፊዎች ናቸው ተብለው የሚጠረጠሩትን ወይም ዝንባሌ አላቸው የሚባሉትን ሁሉ ነቅሶ በማውጣት ለብአዴን ነፍስ ለመዝራት ሙከራ እየተደረገ ነው። እነዚህን ውሳኔዎች ያስፈጽማሉ የተባሉ በጭካኔያቸው ፣ በጎጠኝነታቸውና በንቅዘታቸው የሚታወቁትን የእነሱ ታማኝ ካድሬዎችን ወደ ፊት ለማምጣት በማሰብ ሰሞኑን ሹም ሽር አድርገዋል። ጉልቻ ቢቀያየር ወጥ አያጣፍጥም እንደሚባለው የሰዎች መለዋወጥ የብአዴንን ህልውና ከክስመት የሚታደገው አይሆንም።
ለመሆኑ ብአዴን የህወሀትን ዙፋን ከመጠበቅ በስተቀር ባለፉት 22 አመታት እወክለዋለሁ ለሚለው ህዝብ ምን ሰራ? ብአዴን ባለፉት 22 ዓመታት ከሰራቸው አሳፋሪ ስራዎች መካከል ሰፊው የአገራችን መሬት ለሱዳን ተላልፎ ሲሰጥ የስምምነት ፊርማውን ማስቀመጡ ነው። ከዚህ በተጨማሪ እወክለዋለሁ የሚለው የአማራ ህዝብ ከቦታ ቦታ ሲፈናቀል፣ ለአመታት ህዝቡ በኤድስና በወባ እንደቅጠል ሲረግፍ ፣ ወጣቱ ስራ አጥቶ በአደገኛ እጾች ደንዝዞና ተስፋ ቆርጦ የወጣትነት እድሜውን በከንቱ ሲያሳልፍ ብአዴን ዞር ብሎ ለማየት ፈቃደኛ አልሆነም።
የብአዴን ዙፋን ጠባቂነት የሰለቻቸው የድርጅቱ አባላት በተለያዩ ጊዜያት የውስጥ ትግል ሲያደርጉ ቆይተዋል። ብዙዎች በህወሀትና በተላለኪው ብአዴን የጸጥታ ሀይሎች ተገድለዋል፣ አንዳንዶች ድርጀቱን ለቀው ወጥተዋል፣ አንዳንዶች አሁንም በእስር ላይ ይገኛሉ።
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በብአዴን ውስጥ ብቻ ሳይሆን በመላ አገራችን ስር ነቀል ለውጥ ለማምጣት ፈቃደኝነታቸውን አሳይተው በግንቦት7 ስር ታቅፈው በመንቀሳቀስ ላይ ያሉት ወጣት አባላት የቀድሞ አባሎች የጀመሩትን ትግል በተደራጀና ስርአት ባለው መልኩ ለማስኬድ የጀመሩት ትግል ንቅናቄው በትኩረት የሚከታተለው ነው። ይህ ትግል ተጠናክሮ በሌሎች ድርጅቶችም ተግባራዊ እንዲሆን ግንቦት7 በተለያዩ የኢህአዴግ ድርጅቶች ውስጥ ላሉ አባሎቹ ጥሪውን ያስተላልፋል።
ግንቦት7 መላውን የኢትዮጵያ ህዝብ ከዘረኛው፣ ዘራፊውና ራዕይ አልባው የህወሀት ጎጠኛ አገዛዝ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለመገላገል እና በምትኩ የሁሉም የምትሆን ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን ለመገንባት የጀመረውን ትግል ከመቼውም ጊዜ በላይ አጠናክሮ ቀጥሏል። በዚህ ወሳኝ የትግል ምእራፍ ወቅት የሁሉም ኢትዮጵያዊ ተሳትፎ አስፈላጊ ነው ብሎ ንቅናቄው እንደሚያምን በተደጋጋሚ ሲገልጽ ቆይቷል። በተለይም በኢህአዴግ ድርጅቶች ውስጥ ታቅፈው በመንቀሳቀስ ላይ ያሉ እውነተኛ የስርአት ለውጥ እንዲመጣ የሚፈልጉ ሀይሎች የብአዴን ወጣት የግንቦት7 አባላት እያሳዩት ካሉት እንቅስቃሴ ልምድ በመውሰድ በውስጥ የሚያደርጉትን ትግል አጠንክረው እንዲገፉበት ንቅናቄያችን ጥሪውን ያቀርባል።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!

Wednesday, December 25, 2013

በደቡብ ሱዳን ተገደው የተደፈሩ 4 ኢትዮጵያውያን ሴቶች ጁባ ገቡ

ታህሳስ ፲፬( አስራ አራት )ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በደቡብ ሱዳን የተነሳውን የእርስ በርስ ግጭት ተከትሎ የተደፈሩ 4 ሴቶች የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሆስፒታል በሚገኝበት ጁባ ደርሰው ምርመራ እየተደረገላቸው ነው። ሴቶቹ መደፈራቸውንና ሆስፒታል መግባታቸውን ኢሳት ለማረጋገጥ የቻለ ሲሆን፣ ሴቶቹ በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ ለማወቅ ያደረገው ጥረት በመስመር ግንኙነት የተነሳ ሊሳካለት አልቻለም። ይህ በእንዲህ እንዳለ በደቡብ ሱዳን የኢትዮጵያ አምባሳደር ከውጭ ጉዳይ ሚኒሰትሩ ጋር በመሆን ወደ ኢትዮጵያ መመለሳቸው ታውቋል። አምባሳደሩ በዚህ አስቸጋሪ ሰአት ወደ አገራቸው መመለሳቸውን በአገሪቱ ያሉ ኢትዮጵያውያን ተችተዋል። በሌላ በኩል ግን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቴዎድሮስ አድሀኖም የኢትዮጵያን ስደተኞች በተመለከተ ኢምባሲው በቅርበት ጉዳዩን እየተከታተለ ነው ብለዋል። ሚኒስትሩ ለሱዳን ችግር የኢጋድ አገሮች የሽምግልና ጥረት መጀመራቸውንም ገልጸዋል። በሽምግልና ጥረቱ ስለተገኘው ውጤት ግን ያሉት ነገር የለም። ይህ በእንዲህ እንዳለ በደቡብ ሱዳን የተፈጠረውን የ እርስበርስ ግጭት ተከትሎ ጎሳ ላይ ያነጣጠረ የጅምላ ግድያ እንደተፈፀሙ የሚያሳዩ አዳዲስ መረጃዎች በመውጣት ላይ ናቸው። ጋዜጠኞች ከጁባ የዓይን ምስክሮችን ዋቢ አድርገው እንደዘገቡት ግጭቱን ተከትሎ ከ200 በላይ የሚሆኑ የንዌር ጎሳ ተወላጆች በደህንነት ሀይሎች በጅምላ ተገድለዋል። ሌላ የጁባ ነዋሪም ሲናገር ብዙዎቹ የጸጥታ ሀይሎች ከዲንካ ጎሳ አባላት ስለሆኑ ኑዌሮችን እየለዩ ይገድሉ ነበር ብሏል። ከሳምንት በፊት በጁባ የተቀሰቀሰው ግጭት ወደተለያዩ ቦታዎች ተሸጋግሮ በሪክ ማቻር የሚመሩት አማጽያን “ቦር” እና “ቤንትዩ” የተሰኙ ቁልፍ ከተሞችን ተቆጣጥረዋል። ፕሬዜዳንት ሳልቫኪር የቀድሞ ምክትላቸው መፈንቅለ መንግስት ሊፈፅሞባቸው እንዳሰቡ ክስ ቢያሰሙም፤ ሪክ ማቻር ግን በተቃውሞ የተነሱት በስርዓቱ እየተፈፀመ ባለው ጎሳ ላይ ያነጣጠረ የመብት ረገጣ እና ጥሰት ተከፍተው እንደሆነ በመግለጽ ነው ክሱን ያስተባበሉት። በቀድሞ ሁለት የትግል ጓደኛሞች መካከል በስልጣን ማግስት የተከሰተው ይህ ግጭት በኑዌር እና ዲንካ ጎሳዎች መካከል ሙሉ ጦርነት በማስነሳት ደቡብ ሱዳንን ዳግም መውጫ ወደሌለው የጦርነት አዙሪት ውስጥ እንዳይከታት ከፍተኛ ስጋት ማሳደሩን የቢቢሲ ዘገባ ያመለክታል። በተመሳሳይ ዜና ደግሞ ሰሞኑን በአማጺዎች ቁጥጥር ስር ውላ ነበረችው ቦር በመንግስት ሀይሎች እጅ መውደቋን ቢቢሲ ዘግቧል። የመንግስት ቃል አቀባይ እንደሉት ጦራቸው ከተማዋን ሙሉ በሙሉ ከአማጽያን እጅ አስለቅቀዋል። አማጽያኑንም እግር በግር እየተከተሉ እየወጉዋቸው ነው። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ተወካይ ማምሻውን እንዳስታወቁት ደግሞ በአገሪቱ በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ሳይገደሉ አልቀረም። በተለያዩ አካባቢዎች ሰዎች በጅምላ የተቀበሩባቸውን ቦታዎች ማግኘታቸውን ባለስልጣኑ ገልጸዋል።

ሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤቱን እንዲለቅ ትእዛዝና ማስጠንቀቂያ ተሰጠው::‪

ታህሳስ ፲፬( አስራ አራት )ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ሰማያዊ ፓርቲ ግንፍሌ አከባቢ የሚገኘውን እና በጽ/ቤትነት የሚጠቀምበትን ቢሮ በአስቸኳይ እንዲለቅ ትዕዛዝ ደረሰው። በዛሬው እለት ከሰኣት በኋላ አቶ ሄኖክ የተባሉ አከራዩ ከአራት ግለሰቦች ጋር በመምጣት ፦”ቤቱን ለነዚህ ግለሰቦች ስለሸጥኩላቸው እንድትለቁላቸው” ሲሉ ከውል ውጪ ትዕዛዝ አስተላልፈዋል። ቤቱን ገዛሁት የሚለው ግለሰብ በበኩሉ፦”ቤቱን የኔ ስለሆነ በአስቸኳይ እንድትለቁልኝ፣ ካልሆነ የራሴን እርምጃ እወስዳለሁ” ሲል አመራሮቹ ላይ ዝቷል:: ይህ ግለሰብ በማይመለከተው ጉዳይ በመግባት፦” ከዚህ በፊትም ልቀቁ ተብላችሁ በተደጋጋሚ እንደተነገራችሁ መረጃው አለኝ፤ በቶሎ የማትለቁ ከሆነ እርምጃ ይወሰድባችሁዋል” በማለት በአመራሮቹ ላይ ቁጣ የተቀላቀለበት ዛቻ በመዛት ሄዷል:; ሰማያዊ ፓርቲ ከዚህ ቀደም በመነን አከባቢ ተከራይቶት የነበረውን ጽ/ቤት ገና ሳይገባበት በዝግጅት ላይ እንዳለ የገዢው ፓርቲ ካድሬዎችና እና ቅጥረኞች በተቀናጀ አፈናና ሀይል የተቀላቀለበት እርምጃ ቢሮውን እንዳስለቀቁት ይታወቃል:: ቀደም ሲል ከሰማያዊ ፓርቲ የተነጠቀውን ቢሮ የወሰደው ካድሬም፤ ፔንሲዎን ከፍቶ እየነገደበት እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል። የፓርቲው ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ካለፉት ሳምንታት ጀምሮ ፓርቲያቸውን በውጪ አገራት ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በማስተዋወቅ ላይ እንደሚገኙ ይታወቃል።

ሰበር ዜና]አርቲስት ሚኪያ በሀይሉ አረፈች Artist Mikaya Behailu has passed away

December 25, 2013 download (1)
ድምፃዊ ሚኪያ ባሃይሉ አረፈች !! ሰሞኑን በጨጓራ ህመም ስትሰቃይ እንደነበር እና የሞቷም መንስኤ ይሄው ህመም መሆኑን ምንጮች ገልፀዋል ፡፡ ሚኪያ በመምህርነት ሙያ ያገለገለች በኋላም ወደሙዚቃ በመግባት ሸማመተው በሚል አልበሟ ከፍተኛ እውቅና አግኝታ ያገኘች ወጣት አርቲስት ነበረች ፡፡ ለአድናቂወቿና ለቤተሰቦቿ

Tuesday, December 24, 2013

በቀብሪ ቤያህ እስር ቤት ውስጥ የሞቱ ሰዎች የሉም ሲል የክልሉ ፖሊስ አዛዥ አስተባበሉ

http://ethsat.com/amharic

                                                     
                                                                 The Truth media  

፲፫( አስራ ሦስት )ቀን ፳፻፮ /  ኢሳት ዜና :- የክልሉ ጽህፈት ቤት ፖሊስ አዛዥ  ከጅጅጋ 25 ኪሜ ገደማ በምትገኘዋ ቀብሪበያህ እስር ቤት ውስጥ የሞቱ ሰዎች ስለመኖራቸው ሪፖርት እንዳልደረሰቻው ገልጸዋል። አዛዡ እንዳሉት በክልሉ የሚንቀሳቀሱ ሽብረተኞችን በተመለከተ ከፌደራል መንገስቱ የጸረ ሽብር ግብረሀይል ጋር በጋራ የሚሰሩ በመሆኑ፣ በዚሁ ወንጀል ተጠርጥረው የሚያዙ ካሉ በጋራ የሚታይ ጉዳይ ይሆናል ሲሉ አክለዋል
በጅጅጋ የተከበረውን የብሄር ብሄረሰቦች በአል ምክንያት በማድረግ “መታወቂያ የላቸውም፣ የከተማዋን ገጽታ ያበላሻሉ፣ ከተማዋን ያቆሽሻሉ፣ የጸጥታ ስጋት ደቅነዋል በሚል ከ770 በላይ ሰዎች ቀብሪበያህ በሚባለው ወረዳ ውስጥ በአንድ ክፍል ውስጥ እንዲታሰሩ ከተደረጉት መካከል ከ40 በላይ የሚሆኑት መሞታቸውን ማንነታቸው እንዳይታገለጽ ከጠየቁ የክልሉ ባለስልጣናት ያገኘውን መረጃ በመንተራስ ዘገባ መስራታችን ይታወሳል።
እስረኞቹ የሞቱት በምግብ እጥረትና በእስር ቤቱ ውስጥ በተነሳ የታይፎይድ ( ተስቦ) በሽታ መሆኑን የዜናው ምንጮች ገልጸዋል። ዘመዶች የሞቱባቸውንና ለቅሶ የተቀመጡ ሰዎችን ኢሳት ለማነጋገር ቢሞክርም፣ ሰዎቹ  ለደህንነታቸው በመስጋት ለመናገር ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል።
ሰዎችን ከከተሞች በመውሰድ ያሰሩዋቸው በክልሉ ውስጥ የሚንቀሳቀሱት ልዩ ሚሊሺያ እየተባሉ የሚጠሩት ታጣቂዎች መሆናቸውን ምንጮች አክለው ገልጸዋል። ማንኛውም የሰብአዊ መብት ድርጅት በአካባቢው በመሄድ በቀላሉ ማረጋገጥ የሚችለው ሀቅ ነው በማለት የክልሉ ፖሊስ አዛዥ የሰጡትን ማስተባበያ ውድቅ አድርገዋል። ለሁለት ወራት ያክል ታስረው የነበሩት በተለያዩ ምክንያቶች የታሰሩ የከተማዋ ነዋሪዎች ባለፈው ሳምንት መለቀቃቸውን መዘገባችን ይታወሳል።
                                                             

Sunday, December 22, 2013

ወታደራዊ መኮንኖች የደሞዝ ይጨመርልን ጥያቄ አቀረቡ

ኢሳት ዜና :-የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ከፍተኛ ወታደራዊ መኮንኖች ካለፉት 8 ቀናት ጀምሮ ስብሰባ ላይ ሲሆኑ የደሞዝ ጭማሪ ጥያቄ ዋነኛው የመነጋገሪያ አጀንዳ መሆኑ ታውቋል።
somalia_news-ethiopia_withdraws-2012-1-6ከመቶ አለቃ በላይ ማእረግ ያላቸው ወታደራዊ መኮንኖች ስብሰባዎችን እያካሄዱ ያሉት የጄኔራሎች ስብሰባ ከወር በፊት መጠናቀቁን ተከትሎ ነው። በጄኔራሎቹ ስብሰባ ላይ ለሰራዊቱ የደሞዝ ጭማሪ ጥያቄ ተነስቶ የነበረ ቢሆንም፣ “ሰራዊቱ አሁን የሚያገኘው ደሞዝ ለኑሮው በቂ ነው” የሚል መልስ ከሰራዊቱ ዋና አዛዦች ተሰጥቷል።  በተሰጠው መልስ የተበሳጩት  ጄኔራል ሰአረ መኮንን ስብሰባ ረግጠው ወጥተው እንደነበር ታውቋል። ጄኔራሉን ለማረጋጋት ከፍተኛ ጥረት ተደርጎ እንደነበርም የደረሰን መረጃ ያመለክታል። ጄኔራል ሰአረ ለሰራዊቱ ደሞዝ እንዲጨመር አቋም ከያዙት ከፍተኛ መኮንኖች መካከል አንዱ ናቸው።
ሰሞኑን በመካሄድ ላይ ባለው ከጄኔራል በታች ማእረግ ባላቸው መኮንኖች ስብሰባም   የደሞዝ ጭማሪና የኑሮ ውድነት ዋና አጅንዳ ሆኖ ቀርቧል።
በምስራቅ አካባቢ ባለው እዝ አንዳንድ መኮንኖች ” እኛ ቤተሰቦቻችንን ምግብ አብልተን ለማኖር አልቻልንም፣ እናንተ በሙስና በዘረፋችሁት ገንዘብ ልጆቻችሁን ውጭ አገር ልካችሁ ታስተምራላችሁ” በሚል አለቆቻቸውን በድፍረት መተቸታቸውን የውስጥ ምንጮች ገልጸዋል።   መኮንኖች ያቀረቡትን ጥያቄ የመደረክ መሪዎች ለመመለስ ሲቸገሩ ታይቷል።
መኮንኖቹ ስብሰባቸውን ሲጨርሱ ከተራ ወታደሮች ጋር የሚደረገው ስብሰባ ይቀጥላል ተብሎአል።
ከፍተኛ ቅሬታ እየተስተናገደበት ባለው ስብሰባ፣ ወታደሮቹ እንደ መኮንኖቹ ሁሉ የደሞዝ ጭማሪ ጥያቄ ሊያነሱ ይችላሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ወታደራዊ ምንጮች ገልጸዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ አንድ ሻምበል የወለደውን ልጅ በእሳት ማቃጠሉ ታውቋል። በምስራቅ እዝ የሚገኘው ሻምበል ፈቃዱ በዳዳ ከሳምንታት በፊት በልጁ ላይ ቤንዜን በማርከፍከፍ ያቃጠለው ሲሆን፣ ልጁም ወዲያውኑ ህይወቱ ሲያልፍ አባቱ ደግሞ ቆስሎ ሆስፒታል ተኝቷል። ሻምበል ፈቃዱ በልጁ ላይ ይህን አሰቃቂ እርምጃ ለምን እንደወሰደ አልታወቀም።
 http://www.clickhabesh.com/?p=103432

Friday, December 20, 2013

በደቡብ ሱዳን የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን ለማስወጣት የሚደረግ እንቅስቃሴ የለም ተባለ

http://ethsat.com/amharic


( አስር )ቀን ፳፻፮ /  ኢሳት ዜና :-  በደቡብ ሱዳን የተነሳውን የእርስ በርስ ግጭት ተከትሎ በአገሪቱ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የደህንነታቸው ሁኔታ አሳሳቢ ቢሆንም መንግስት እስካሁን  እርምጃ እየወሰደ አለመሆኑ ታወቀ።
የኢሳት የጁባ ወኪል እንደገለጹት አብዛኛው አገሮች ዜጎቻቻውን እያወጡ ነው ። ኬንያና ኡጋንዳ አውቶቡሶችን በመላክ ፣ አሜሪካና እንግሊዝ ደግሞ ወታደራዊ አውሮፕላኖችን በመላክ ዜጎቻቻውን እያወጡ ነው። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ንብረት የሆነ አውሮፕላን ጁባ ማረፉን ተከትሎ አንዳንድ ኢትዮጵያውያን ወደ አገራቸው ለመመለስ ተስፋ አድርገው የነበረ ቢሆንም፣ አውሮፕላኑ ግን ቻይናዎችን ብቻ ጭኖ መመለሱ ታውቋል።  ኢሳት ከአየር መንገዱ ለማረጋገጥ እንደቻለው የቻይና መንግስት ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ቻርተር አውሮፕላን በመከራየት  በነዳጅ ማውጣት ስራ ላይ የተሰማሩ ዜጎቹን ወስዷል።
እንዲሁም   ለሽምግልና ጁባ የሄዱትን የኢትዮጵያን ባለስልጣናት በማሳፈር ጁባ ያረፈ አንድ የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን፣ ባለስልጣኖችን ካወረደ በሁዋላ ትኬት ቆርጠው ለመውጣት ይጠባበቁ የነበሩ ኢትዮጵያውያንን ሳይጭን ባዶውን ተመልሷል። ኢትዮጵያውያኑ የኬንያንና የኡጋንዳን አየር መንገዶችን ለመጠቀም ጥረት እያደረጉ ቢሆንም፣ አየር መንገዶቹ ከፍተኛ ዋጋ በመጠየቃቸው ትኬቶችን ለመግዛት አልቻሉም።
ኢሳት ለማረጋገጥ ባይችልም ሶሰት ኢትዮጵያውያን ሴቶች መደፈራቸውን የሚያመለክት ዜና ደርሶታል። አንዳንድ ኢትዮጵያውያንም ንብረታቸውን ተዘርፈው በጁባ መንገዶች ላይ ያለ ደጋፊ ሲዞሩ እንደሚታይ ወኪላችን ገልጿል።
የኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ ኡጋንዳ፣ ጅቡቲ  እና ሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ላለፉት ሁለት ቀናት በጁባ ተገኝተው ሁለቱን ሀይሎች ለመሸምገል ጥረት እያደረጉ መሆኑም ታውቋል። ደ/ር ቴዎድሮስ አድሀኖም ሁለቱንም ሀይሎች ለማቀራረብ ከፕሬዚዳንቱ ጥሩ ምላሽ ማግኘታቸውን ገልጸዋል።
ቦር የተባለው አካባቢ በአማጽያን እጅ የወደቀ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ ድንበር በሆነው አኮቦ በትናንትናው እለት ጦርነት ተከፍቷል። ዛሬ ደግሞ ማላኪ፣ ዋው እና ባንቲዩ በተባሉት አካባቢዎች ጦርነት ተከፍቷል። ባንቱዊ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጽህፈት ቤት የሚገኝበት ሲሆን፣ በርከታ የዲንቃ ተወላጆች በጽህፈት ቤቱ ግቢ ውስጥ መግባታቸው ታውቋል። በጁባ የኑዌር ተወላጆች ከዲንቃ ጎሳዎች ጥቃት ሊሰነዘር ይችላል ብለው በተመድ ጽ/ቤት ውስጥ ሲጠለሉ፣ በቤንቲዩ ደግሞ በተቃራኒው ዲንቃዎች ተጠልለዋል።
ፕሬዚዳንት ኦባማ አዲሲቷ አገር ወደ እርስ በርስ ጦርነት ልትገባ እንደምትችል አስጠንቅቀዋል። እስካሁን ባለው አሀዝ ከ500 ያላነሱ ሰዎች ተገድለዋል።

Thursday, December 19, 2013

ከወያኔ ክፋትና እብሪት እንጂ ፍትህ አይጠበቅም

http://www.ginbot7.org
ወያኔ ባለፉት ሃያ ሁለት አመታት የአገራችንን የፍትህ ተቋሞች አንዴ አንደ ቂም መበቀያ ሌላ ግዜ ደግሞ እንደ ማጥቂያ መሳሪያ እየተጠቀመባቸዉ የፖለቲካ ተቀናቃኞቹንና ጥርስ የነከሰባቸዉን የህብረተሰብ አባላት እያሰረ፤ እያሳደደና እየገደለ ከርሞ ዛሬ ላይ ደርሷል። በተለይ ከግንቦት 1997ቱ ምርጫ በኋላ ወያኔ ብዕርና ወረቀት ይዘዉ በሃሳብና በአመክኖ የታገሉትን ሰላማዊ ዜጎች “ሽብርተኞች”፤ ድምጻችን ይሰማ ብለዉ የመብትና የነጻነት ጥያቄ አንግበዉ በሰላማዊ መንገድ የታገሉትን ኢትዮጵያዉያን የእስልምና እምነት ተከታዮች ደግሞ “አክራሪዎች” እያለ ፍርድ ቤት በማቅረብ በፍትህ ተቋሞች በኩል የፖለቲካ ዉሳኔ በማሳለፍ ሠላማዊ ዜጎችን ለረጂም ግዜ እስርና እንግልት ዳርጓል።
ወያኔ ለኢትዮጵያና ለዜጎቿ ደንታ የሌለዉ እና ከስህተቱ የማይማር የግብዞችና የዘረኞች ስብስብ ስለሆነ አሁንም የአገሪቱን የፍትህ ተቋሞች እንደ ማጥቂያ መሳሪያ እየተጠቀመ የኢትዮጵያን ህዝብ በፍርሃት ጨለማ ዉስጥ ሸብቦ እየገዛ ለመኖር የቆረጠ ይመስላል። ባለፈዉ ሳምንት አጋማሽ ላይ የወያኔ አገዛዝ ከአንድ አመት ተኩል በላይ እስር ቤት ዉስጥ አጉሮ ያቆያቸዉን የድምጻችን ይሰማ መሪዎች ከፊሎቹን በነፃ ተለቅቀዋል የሚል ከፊሎቹን ደግሞ ተከላከሉ የሚል ትርጉም የለሽ ብይን ሰጥቷል። በህወሀት ታጋዮች የተሞላዉ ፍርደ ገምድሉ የወያኔ ፍርድ ቤት እንኳን ተከሳሾቹ በተከሰሱበት ሽብር የመፈጸም ወንጀል ምንም አይነት ማስረጃ አልተገኘባቸዉም ሲል አገዛዙ ግን የፖለቲካ ክንዱን በመጠቀም ማስረጃ ያልተገኘባቸዉን ሠላማዊ ዜጎች የተከሰሱበትን መሰረተ ቢስ ክስ ተከላከሉ የሚል የፖለቲካ ዉሳኔ ሰጥቷል።
የወያኔ አገዛዝ የሙስሊሙን ህብረተሰብ የመፍትሄ አፈላላጊ ቡድን መሪዎች ፍርድ ቤት ያቀረባቸዉ ለምዕራባዉያን ለጋሾቹና ለአለም አቀፍ አበዳሪ ድርጅቶች ኢትዮጵያ ዉስጥ ፍትህ ያለ ለማስመሰል ነዉ እንጂ ወያኔ የድምጻችን ይሰማ መሪዎችን የፈረደባቸዉ ያሰራቸዉ ቀን ነዉ። የወያኔ የፍትህ ታሪክ በግልጽ እንደሚያሳየን ወያኔ ግለሰቦችን የሚያስረዉ ለክስ የሚያበቃ ማስረጃ አግኝቶባቸዉ አይደለም፤ ይልቁንም ወያኔ ማስረጃዎችን እየፈበረከ ለፍረድ ቤቶች የሚያቀርበዉ ግለሰቦችን ካሰረና ሰብዓዊ መብታቸዉን ከገፈፈ በኋላ ነዉ። ለምሳሌ የድምጻችን ይሰማ መሪዎችን አስሮ ብዙም ሳይቆይ የእነዚህን ሰላማዊ ዜጎች ተክለ ሰዉነት ጥላሸት የቀባና ግለሰቦቹን ያለ ማስረጃ ወንጀለኛ አድርጎ የፈረጀዉን “ጂሐዳዊ ሀረካት” የሚል የፈጠራ ድራማ ሰርቶ ለህዝብ አቅርቧል።
የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሽብር በመፈጸም ወንጀል ተጠርጥረዉ የቀረቡለትን ግለሰቦች በተከሰሱበት ወንጀል ማስረጃ አላገኘሁባቸዉም ካለ በኋላ ሁሉንም በነጻ አለማሰናበቱ የሚያሳየን የወያኔ ፍርድ ቤቶች ከፖለቲካ ተፅዕኖ ነጻ አለመሆናቸዉን ብቻ ሳይሆን፤ ኢትዮጵያ ዉስጥ ፍርድ ቤቶች የገዢዉ ፓርቲ የማጥቂያ መሳሪያዎች መሆናቸዉን ጭምር ነዉ። የወያኔን አገዛዝ ከሌሎች አምባገነኖች ለይቶ አደገኛ የሚያደርገዉና በምዕራባዉያን መንግስታትና በቀላጤዎቻቸዉ እንዲወደስ ያደረገዉም ይሄዉ አገዛዙ የሚቃወሙትን ኃይሎች የሚያጠፋቸዉ እንደሌሎቹ አምባገነኖች በግልጽ ሳይሆን በህግ ሽፋን ዉስጥ በስዉር መሆኑ ነዉ።
የወያኔዉ ፍርድ ቤት በተመሳሳይ ወንጀል ተከስሰዉ የቀረቡለትን ነገር ግን ምንም መረጃ ያላገኘባቸዉን የድምጻችን ይሰማ መሪዎች ገሚሶቹን በነፃ ለቅቆ የተቀሩትን ጥፋተኛ አለመሆናችሁን አረጋግጡ ብሎ መወሰኑ የወያኔን ሁለት እኩይ አላማዎች ያሳየናል። የመጀመሪያዉ የወያኔ አላማ በአላማቸዉ ጸንተዉ የቆሙትን የድምጻችን ይሰማ መሪዎች መከፋፈል ሲሆን፤ ሁለተኛ አላማዉ ደግሞ የኢትዮጵያ ፍርድ ቤቶች የቀረቡላቸዉን የክስ መዝገቦች በሚገባ አጣርተዉ ዉሳኔ የሚሰጡ መሆናቸዉን ለአለም አቀፉ ህብረተሰብ ለማሳየት ነዉ።
የኢትዮጵያ ህዝብ ግን እንደዚህ አይነቶቹን የወያኔ እኩይ ተግባሮች ካወቀ ዉሎ አድሯል፤ ስለሆነም ከወያኔ ፍትህ ጠብቆ አያዉቅም፤ ወያኔ የክፋትና የበቀል ምንጭ ነዉና ለደፊትም አይጠብቅም። የድምጻችን ይሰማ መሪዎችም ሆኑ ከእነሱ በፊት በግፍ ታስረዉ መከራቸዉን የሚያዩት የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎች፤ ጋዜጠኞችና የሲቪክ ማህበራት መሪዎች የታሰሩት ለቆሙለት የፍትህ፤ የነጻነትና የእኩልነት አላማ እንደ አለት ጸንተዉ በመቆማቸዉ ነዉ። እነዚህ ጀግኖች የታሰሩለት አላማ የሁላችንም አላማ ነዉና ፍትህ፤ እኩልነትና ነጻነት የጠማን ኢትዮጵያዉያን ክንዳችንን አስተባብረን የችግሮቻችን ሁሉ ምንጭ በሆነዉ በወያኔ ስርዐት ላይ ክንዳችንን በጋራ እናንሳ!
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!

  POSTED BY SAMUALE TEWELDE

US prosecutor defends arrest and strip-search of Indian diplomat


ኦባንግ ከደቡብ ሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚ/ር ጋር ተነጋገሩ

http://www.goolgule.com/obang-spoke-with-south-sudan-foreign-affairs-minister/

“በራችሁን ዘግታችሁ እርቅ አውርዱ”
Picture2
* “ባለውለታችሁ የኢትዮጵያ ህዝብ አዝኖባችኋል፣ አርቃችሁ እዩ”
“በትግሉ ወቅት ለነጻነት ስትዋደቁ ኢትዮጵያ በጋምቤላ አኙዋክ ምድር ላይ ሙሉ ከለላና ዋስትና በመስጠት ያበረከተችው አስተዋጽኦ የሚረሳ ነው? ከነጻነት ታጋዮችችሁ ጎን በመሰለፍ ብረት ያነሱ የአኙዋክ ኢትዮጵያውያን ልጆች መስዋዕትነት ይዘነጋችኋል? አሁን ድረስ የትግሉ የመስዋዕትነት ቁስላቸው ያልዳነ የአኙዋክ ልጆች እንዳሉ ትዘነጋላችሁ?” በማለት የተናገሩት የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ ዋና ዳይሬክተር አቶ ኦባንግ ሜቶ /ጥቁሩ ሰው/ ናቸው።
በታላላቅ መድረኮችና በበርካታ ኢትዮጵያውያን ዘንድ ተሰሚነታቸውና ስብዕናቸው እየጎላ የሄደው ጥቁሩ ሰው ለጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ እንደተናገሩት፣ ከላይ የተገለጸውን ህሊና የሚፈታተን ጥያቄ ያቀረቡት ለደቡብ ሱዳን የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ባርናባ ማሪያል ቤንጃሚን ነው። ለረዥም ሰዓት ጊዜ ወስደው ውይይት ማድረጋቸውን ተከትሎ የጎልጉል የአሜሪካ ዘጋቢ እንደዘገበው አቶ ኦባንግ ዶ/ር ባርናባን ያገኟቸው አሜሪካ ዋሽንግተን ዲሲ ነበር።
በጁባ የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ መደረጉ ይፋ ከተደረገበት አንድ ቀን በፊት አስቀድሞ በተያዘ የውይይት መርሃ ግብር የተገናኙት ዶ/ር ባርናባና አቶ ኦባንግ በርካታ ወቅታዊ ጉዳዮችን አንስተው መነጋገራቸው ታውቋል። አቶ ኦባንግ የደቡብ ሱዳን የነጻነት ትግል ወቅት ኢትዮጵያ በመንግስት ደረጃ የሰጠችውን ሙሉ ድጋፍና፣ ድንበር ሳይከልላቸው በሁለቱም አገራት የሚገኙት የአኙዋክ ልጆች ትግሉን የነፍስ ዋጋ በመክፈል መደገፋቸውን በማስታወስ በውይይቱ ወቅት ያነሱት ያለ ምክንያት አልነበረም።
“በጆን ጋራንግ ይመራ የነበረው ትግል ፍሬ አፍርቶ ደቡብ ሱዳን ነጻ ስትወጣ የማይረሳ ውለታ ለሰራቸው ኢትዮጵያና የአኙዋክ ልጆች የተከፈላቸው ብድር አሳዛኝና የወደፊቱን ጊዜ ያላገናዘበ ነው” በማለት በውይይቱ ስለተነሱ ነጥቦች ማብራሪያ የሰጡት አቶ ኦባንግ፣ “ለህዝቦች ነጻነትና ለሰብአዊ መብት መከበር የታገለ ድርጅትና አመራሮች ለነጻነታቸው የተከፈለላቸውን የደም ዕዳ ያወራረዱትና እያወራረዱ ያሉት ከወያኔ መሪዎች ጋር በማበር ከለላ የጠየቁ ህጋዊ ስደተኞችን እያፈኑ ለወያኔ አሳልፎ በመስጠት መሆኑ አሳዝኖኛል። ኢትዮጵያዊያን አዝነዋል” በማለት ነበር።
ህጋዊ ከለላ የጠየቁ ስደተኞች ቶርቸር እንዲደረጉ፣ እንዲገደሉ፣ እንዲታሰሩና ኢሰብአዊ ግፍ እንዲፈጸምባቸው ለአምባገነኖች አሳልፎ መስጠት ዘግይቶም ቢሆን ዋጋ እንደሚያስከፍል አቶ ኦባንግ አስረግጠው ተናግረዋል። በ1993 የአኙዋክ ጄኖሳይድ /የጅምላ ጭፍጨፋ/ ሸሽተው በስደት ደቡብ ሱዳን የገቡ የአኙዋክ ልጆችን ለገዳዩ የወያኔ አንጋች ሃይል ማስረከብ መቆም እንዳለበት ያሳሰቡት አቶ ኦባንግ “ይህንን ተግባር የፈጸሙትም ቢያንስ ዓለም አቀፋዊውን ህግ ተላልፈዋልና ሊጠየቁ ይገባል። እርስዎም ይህንኑ የማስፈጸም ሃላፊነት ይኖርብዎታል” በማለት ለውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩ አሳስበዋል።
የአኙዋክና የበኩር ልጆችና የደቡብ ሱዳን ግንኙነት ከድንበር ያለፈ የደም ትስስርና ኢትዮጵያ የማይረሳ ውለታ በመክፈል ያከበረችው ውህደት በመሆኑ መንግስታቸው ቆም ብሎ ሊያስብ እንደሚገባው አቶ ኦባንግ ምክር አዘል መልዕክት ማስተላለፋቸውን አመልክተዋል። ኢትዮጵያ አስተማማኝ ከለላና ዋስትና በመስጠት የፈጸመችውን ሊዘነጋ የማይችል ተግባር አለማክበር ለወደፊቱ ወዳጅ የሚያሳጣ ብድር ለራስ የማስቀመጥ ያህል እንደሆነም በወጉ እንዲገነዘቡ ሚኒስትሩን ተማጽነዋል።
photoአምባገነኑና በህዝብ የሚጠላው የህወሃት አገዛዝ እድሜ አሁን ካለው ትውልድ እድሜ በላይ ዘሎ የሚሄድ ባለመሆኑ በኢትዮጵያ ጉዳይ ያገባናል የሚሉ የፖለቲካ ድርጅቶችን ማቅረብ፣ መተዋወቅና መልካም ግንኙነት መመስረት ለወደፊቱ ጠቃሚ መሆኑንም አስረድተዋል። እርሳቸው በዋና ዳይሬክተርነት የሚመሩት ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄም /አኢጋን/ ከተመሰረተበት ዓላማ አንጻር የደቡብ ሱዳን መንግሥት ህወሃት/ኢህአዴግን ለማስደሰት ሲል ኢትዮጵያዊያን ላይ ፈጸመውና እየፈጸመ ባለው ተግባር ያዘኑ ወገኖች የቀድሞውን የፍቅር መንገድ እንዲከተሉ አበክሮ እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።
ሕዝብ ያልወደደው መንግስትና ህዝብ ያልተቀበለው ኢንቨስትመንት መጨረሻው ኪሳራ በመሆኑ የደቡብ ሱዳን መንግስት ሊጠነቀቅ እንደሚገባው አቶ ኦባንግ ለውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ነግረዋቸዋል። ከደቡብ ሱዳን ተነስቶ በጋምቤላ አድርጎ ወደ ኬኒያና ጅቡቲ ይዘረጋል የተባለው የነዳጅ ማስተላለፊያ ቱቦ ሕዝብን በመግፋትና በመበደል ከቶውንም ተግባራዊ ሊሆን እንደማይችል ያለማቅማማት ጠቁመዋል።
ህዋሀት በጋምቤላ ንጹሃንን ከቀያቸው በጠመንጃ ሃይል በማባረር፣ መሬታቸውን በሳንቲም ቸብችቦ፣ የህይወታቸው ዋስትና የሆነውን ደናቸውን አስጨፍጭፎ፣ ለምን በማለት የጠየቁትን አስሮና ገድሎ ያቋቋመው ኢንቨስትመንት በዜሮ መጣፋቱን ለአብነት ጠቅሰው ማስረዳታቸው የጠቆሙት ጥቁሩ ሰው “ኢንቨስትመንት መልካም ነው። ህዝብ ካልተቀበለው ተግባራዊ ሊሆን አይችልም። ህዝብ ይሁንታ የማይሰጠው ኢንቨስትመንት ፍሬ አያፈራም። ከውስጥም ከውጪም ያላችሁን ግንኙነት መርምሩ። ያዘኑባችሁ ተበራክተዋል” ሲሉ መክረዋል።
በአዲስ የምትቋቋመው “አዲሲቷ ኢትዮጵያ” ለደቡብ ሱዳን ወንድምና እህቶች ጭምር ቦታ በማዘጋጀት መሆኑንን አቶ ኦባንግ አረጋግጠው “በሌላ በኩል ደግሞ በአሁኑ ወቅት ስጋት ውስጥ መሆናቸውን ተናግረዋል። ለዲሞክራሲ መከበርና ለነጻነት በተከፈለው መስዋዕት የተገኘውን ድል የደቡብ ሱዳን መንግስት በአግባቡ እየተጠቀመበት አለመሆኑን አቶ ኦባንግ ለውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩ ገልጸውላቸዋል። አዲሲቷ ደቡብ ሱዳን ከድል በኋላ የትግሉን መሐላ ሙሉ በሙሉ ረግጣለች በማለት መሪዎቹን ወቅሰዋል።
ከድል በኋላ በደቡብ ሱዳን በርካታ ችግሮች መከሰታቸውን በመዘርዘር የማስጠንቀቂያ ምክር መሰንዘራቸውን ያመለከቱት አቶ ኦባንግ “አሁን ባለው ሁኔታ በደቡብ ሱዳን ባሉ ሃያ አንድ ጎሳዎች መካከል ቀውስ መፈጠሩ አይቀርም። ስለዚህ በራችሁን ዘግታችሁ እርቅ አውርዱ። በቀደሙት ሰማዐታቶች ደምና አጥንት ላይ ዴሞክራሲን መስርቱ። ይህንን ካላደረጋችሁና አሁን በያዛችሁት የአምባገነንነትና የአንድ ሰው ወይም ጎሣ የበላይነት መንገድ ከቀጠላችሁ ጣጣው ወደኛም ያመራል” ሲሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩን አስጠንቅቀዋቸዋል። አሁን ያለው የውስጥ ሽኩቻ መልኩን ሳይቀይር መፍጠን እንደሚገባቸውም አስገንዝበዋቸዋል። (አቶ ኦባንግ ይህንን ለውጭ ጉዳይ ሚ/ሩ የተናገሩት እሁድ መፈንቅለ መንግሥት ከመሞከሩና አሁን ደግሞ በዘር /ጎሣ/ መስመር ተከፋፍለው ደቡብ ሱዳናውያን መጫረስ ከመጀመራቸው አንድ ቀን በፊት ነበር)
ambassador 1
አቶ ኦባንግ በአሜሪካ የደቡብ ሱዳን አምባሳደር ጋር
በደቡብ ሱዳን እውነተኛ እርቅ ለማውረድ የአኙዋክ የፍትሕ ምክርቤት አንድ ግብረ ሃይል ወደ ጁባ እንደሚልክ መረጃ እንዳላቸው የጠቆሙት አቶ ኦባንግ በውይይቱ ወቅት ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ቀና ምላሽ ማግኘታቸውን አመልክተዋል። በመጨረሻም አቶ ኦባንግ የሚመሩት ድርጅት ኢትዮጵያ ውስጥ የእርቅ ደጆች የሚከፈቱበት አግባብ ላይ ከሚመለከታቸው ተጽዕኖ አድጊራዎችና አቅሙ ካላቸው አካላት ጋር እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸውላቸዋል። በማያያዝም “እኛ ሩቅ እያየን እየሰራን ነው። እኛ በስፋት እያሰብን በመራመድ ላይ ነን። በስፋት አስበን፣ ሩቅ እያየን ስንሰራ እናንተንም አንዘነጋም። በተቃራኒው እናንተ ለነጻነታችሁ የተዋደቁላችሁን የራሳችሁን ዜጎች እያነቃችሁ ለወያኔ አሳልፋችሁ ትሰጣላችሁ። ደም ያፈሰሱላችሁንና አጥንታቸውን የከሰከሱላችሁን ውድ ዜጎች ሳትታረቁ በምድራቸው ላይ ቱቦ ዘርግታችሁ ብር ልታመርቱ ታቅዳላችሁ። ይህ ከቶውንም ጤነኛ አካሄድ አይደለምና ህዝብን አስቀድሙ። አብረን እንስራ። ይህ መልካም ጅምር ነው” በማለት መሰናበታቸውን አቶ ኦባንግ ለጎልጉል ተናግረዋል።
የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ ዋና ዳይሬክትር አቶ ኦባንግ ሜቶ ከደቡብ ሱዳን የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ባርናባ ማሪያል ጋር ለመወያየት የቻሉት ሚኒስትሩ አሜሪካ ከመምጣታቸው በፊት በኤምባሲያቸው አማካይነት አስቀድሞ በተያዘ መርሃ ግብር መሰረት እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል። በውይይቱ ወቅት ሚኒስትሩ ስለ ሰጡት አስተያየትና ምላሽ አቶ ኦባንግ በዝርዝር ለመናገር አልፈለጉም። አቶ ኦባንግ በትውልድ አኙዋክ ቢሆኑም እርሳቸው የሚመሩት ድርጅት /አኢጋን/ ኢትዮጵያውያን ከአገራቸው ውጭ በስደት በሚሰቃዩበት ቦታ ዘር፣ ቀለም፣ ጎሣ፣ ቋንቋ፣ ወዘተ ሳይለይ ፈጥኖ በመድረስ እርዳታ በማድረግ እርሳቸውም በተመሳሳይ ተግባር ተጠምደው በቅንነት በማገልገል እንደሚገኙ ይታወቃል፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ የእርቅ ደጆች እንዲከፈቱ አግባብ ካላቸውና አቅሙ ካላቸው ክፍሎች ጋር እየሰራን ነው በማለት አቶ ኦባንግ ለሚኒስትሩ የገለጹላቸውን ሃሳብ እንዲያብራሩ ከጎልጉል ተጠይቀው “ሁሌም የእርቅ ደጆች እንዲከፈቱ እንሰራለን። ይህ የጋራ ንቅናቄውና አርቀው የሚመለከቱ ዜጎች ሁሉ እምነት ነው። ብዙ ስራ እየሰራን ነው። ስንጨብጠውና ለህዝብ ሪፖርት የምናቀርብበት አሳማኝ ጊዜ ላይ ስንደርስ ብቻ ይፋ እናደርጋለን። ስራው በባህሪው ከንግግር በመቆጠብ ተግባር ላይ ማተኮርን ስለሚጠይቅ እኛም ባናወራው ጊዜው ሲደርስ ሁሉም በየፊናው የሚገልጸው ይሆናል። ስራው ሳይሰራ ፕሮፓጋንዳው ከቀደመ በሁሉም ወገን ተዓማኒነትን የማጣትና የመጣል አደጋ አለው። የኢትዮጵያ ህዝብ ተግባር የናፈቀው ይመስለኛል” የሚል ድፍን መልስ ሰጥተዋል።
 POSTED BY SAMUALE TEWELDE